መጋባት በሁሉ ዘንድ ክቡር መኝታውም ንጹሕ ይሁን፤ ሴሰኞችንና አመንዝሮችን ግን እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል። (ወደ ዕብራውያን 13፥4)
በመጀመሪያ ደረጃ እግዚአብሔር ጋብቻን በሁሉ ዘንድ ክቡር ይሁን ነው ያለው በሁሉ ዘንድ ሲል በሴቷም በወንዱም በእስልምናውም በክርስትናውም በማንኛውም የሰው ዘር ሊከበር ይገባዋል ነው የሚለው እንዲሁ እንደቀልድ የሚታይ ነገር አይደለም እንደቀልድ ዛሬ ተገብቶበት ነገ የሚወጣበት እንደዘበት የሚታይ ጉዳይ አይደለም ነው የሚለን ።
ሌላው ደግሞ ጋብቻ በአንድ ወንድና በአንዲት ሴት መካከል (ይህ ሃሳብ ሊተኮርበት የሚገባው ነው) የሚፈጸም የመንፈስ የነፍስ እና የስጋ ጥምረት ያለበት ነው ይህም ጋብቻ በሁለት ተቃራኒ ጾታ መሃከል የሚፈጸም እና ዘለቄታ ያለው በእግዚአብሔር በቅዱሳን መላአክቱና እና በሰው ፊት የሚደረግ የቃልኪዳን ትስስር ያለበት ስርዓት ነው ።
ዛሬ ዛሬ እንደምናየው ግን የጋብቻን ክቡርነት በዘነጉና ጋብቻ እንዴት እንደተጀመረ ባልተረዱ ግለሰቦችና የጋብቻ አስፈጻሚ ድርጅቶች እንዲሁም የሃይማኖት ድርጅቶች ውስጥ የሚፈጸመው ቅጥ ያጣ እና ስርዓት የሌለው ወንድና ወንድን እንዲሁም ሴትና ሴትን እያጣመሩ ጋብቻን የመሰረቱ የሚመስላቸው ግለሰቦችም ሆኑ ድርጅቶች በምድር ላይ ጥፋትን እንጂ መልካም የሆነን ስርዓት እየፈጽሙ ላለመሆናቸው ሊረዱት ይገባቸዋል። እነዚህን ግለሰቦች ደግሞ እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል ምክንያቱም የእግዚአብሔር ቃል እንዲህ ይላልና ( … ወይስ ዓመፀኞች የእግዚአብሔርን መንግሥት እንዳይወርሱ አታውቁምን? አትሳቱ፤ ሴሰኞች ቢሆን ወይም ጣዖትን የሚያመልኩ ወይም አመንዝሮች ወይም ቀላጮች ወይም ከወንድ ጋር ዝሙት የሚሠሩ ወይም ሌቦች ወይም ገንዘብን የሚመኙ ወይም ሰካሮች ወይም ተሳዳቢዎች ወይም ነጣቂዎች የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም። 1 ቆሮ 6 : 9-10)
ሴሰኞችንና አመንዝሮችን እግዚአብሔር ከፈረደባቸው ስርዓቱን እያስፈጸሙ ያሉትም ከዚህ ፍርድ የሚያመልጡበት መንገድ አይታየንም ስለዚህ ይህንን ስርዓት ከማስፈጸም ሊታቀቡ ይገባቸዋል አንላለን።
ከዚህ የባሰው የጥፋቶች ሁሉ ጥፋት ደግሞ ይህንን ስርዓት መንግስት ስለፈቀደውና በሕግ ስለተደገፈ ብቻ እግዚአብሔር የፈቀደው ያህል በእግዚአብሔር እናምናለን የሚሉና እግዚአብሔርን እናገለግላለን የሚሉ ግለሰቦችና የሃይማኖት ድርጅቶች የተቃውሞ ድምጻቸውን ያለማሰማታችውና ዝም የማለታቸው ጉዳይ ስርዓቱን ተስማምተው መቀበላቸውን የሚያሳይ እንጂ ሌላ ምንም ሊሆን እንደማይችል እንገነዘባለን። ትንሽ ቆይቶም እነዚሁ ግለሰቦች ስርዓቱን ለመፈጸም ወይም ጋብቻን ለመፈጸም ወደቤተክርስቲያን ቢመጡ የሚሰጣቸው ምላሽ ምን ሊሆን እንደሚችል መዘንጋት የለብንም ምክንያቱም አስቀድመን የተቃውሞ ድምጻችንን አላሰማንምና ።
ይህንን ስርዓት እያስፈጸሙ ያሉና ለማስፈጸም ችግር እንደሌለበትና የማያስጠይቃቸው የመሰላቸው ቤተአምልኮዎች ከእግዚአብሔር ሳይሆን ከአባታቸው ከዲያብሎስ ዘነድ የተላኩ የጥፋት መልእክተኞች መሆናቸውን መዘንጋት የለብንም ።
ስለዚህ በማስጠንቀቅም ይህንን ልላችሁ እወዳለሁ ራሳችሁን ብትመረምሩና ከየት እንደወደቃችሁ ብታስቡና ንስሐ ብትገቡ የትሻለ ነው እላለሁ። በትያጥሮንም ወዳለው ወደ ቤተ ክርስቲያን መልአክ እንዲህ ብለህ ጻፍ፦ እንደ እሳት ነበልባል የሆኑ ዓይኖች ያሉት በእቶንም የነጠረ የጋለ ናስ የሚመስሉ እግሮች ያሉት የእግዚአብሔር ልጅ እንዲህ ይላል፦ ሥራህንና ፍቅርህን እምነትህንም አገልግሎትህንም ትዕግሥትህንም ከፊተኛውም ሥራህ ይልቅ የኋለኛው እንዲበዛ አውቃለሁ። ዳሩ ግን፦ ነቢይ ነኝ የምትለውን ባሪያዎቼንም እንዲሴስኑና ለጣዖት የታረደውን እንዲበሉ የምታስተምረውንና የምታስተውን ያችን ሴት ኤልዛቤልን ስለምትተዋት የምነቅፍብህ ነገር አለኝ፤ ንስሐም እንድትገባ ጊዜ ሰጠኋት ከዝሙትዋም ንስሐ እንድትገባ አልወደደችም። እነሆ፥ በአልጋ ላይ እጥላታለሁ፥ ከእርስዋም ጋር የሚያመነዝሩትን ከሥራዋ ንስሐ ባይገቡ በታላቅ መከራ እጥላቸዋለሁ ልጆችዋንም በሞት እገድላቸዋለሁ፤ አብያተ ክርስቲያናትም ሁሉ ኵላሊትንና ልብን የምመረምር እኔ እንደ ሆንሁ ያውቃሉ፥ ለእያንዳንዳችሁም እንደ ሥራችሁ እሰጣችኋለሁ። (ራእይ 2:18 – 23)
ካሱ ቦስተን