የዘላለም ህይወት እንዳለን እርግጠኛ ነን ?

ክፍል 6

የእግዚአብሔር ልጅ መሆን !

በክፍል 5 ንባባችን ላይ ክርስቶስ ቅጣታችንን እንደተቀበለ ተመልክተናል። ክርስቶስ ስለእኛ ሲል በመስቀል ላይ እስከሞት ድረስ ያደረሰው እግዚአብሄር ለእኛ ያለውን ታላቅ ፍቅር መግለጫ እንደሆነ እናስተውል፤ በሌላ መልኩ ደግሞ ስንመለከተው አንድ የሚያስገኝልን ትልቅ የእግዚአብሄር ልጅነት ስልጣን ነው። በመስቀል ላይ የሞተልንን ጌታ ኢየሱስን አምነን የዘላለም ህይወት ወራሽ ከመሆናችን ጋር የምንወርሰው የልጅነት ስልጣን እንደሆነ በገላቲያ 3፡26-27 እንዲህ ይላል፡- ‹‹በእምነት በኩል ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጆች ናችሁና፤››፡፡ ሁላችን የእግዚአብሔር ልጆች የመሆን ፍላጎት ቢኖረንም ይህ ሊሳካ የሚችለው በእምነት በኩል እንደሆነ ጥቅሱ ያስረዳል፡፡ በክርስቶስ ላይ ያለን እምነት ነው የእግዚአብሔር ልጆች እንድንሆን የሚያደርገን፡፡

ዮሐንስ 1፡12-13 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ለተቀበሉት ሁሉ ግን፥ በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው፤››፡፡ ይህ ጥቅስ የእግዚአብሔር ልጅነት ስልጣን የተሰጣቸው እነማን እንደሆኑና ከእግዚአብሔር መወለድ ማለት ምን ማለት እንደሆነ ይነግረናል፡፡ የልጅነት ስልጣኑ የተሰጠው ክርስቶስን ለተቀበሉ ሲሆን ይህን የሚያደርጉ አማኞች ከእንግዲህ ወዲያ ፍጥረታዊ ሰዎች ብቻ እንዳልሆኑ ጥቅሱ ያበስራቸዋል፡፡

የእግዚአብሔር ልጅና ቤተሰብ ለመሆን ዳግም መወለድ ይኖርብናል፡፡ ጌታችን በዮሐንስ 3፡3 ላይ እንዲህ ያለ ማስጠንቀቂያ ያስተላልፍልናል፡- ‹‹ኢየሱስም መልሶ:- እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም አለው››፡፡ በመቀጠል በዮሐንስ 3፡5 ላይ እንዴት ይህ ዳግም ልደት እንደሚከናወን ያስረዳናል፡- ‹‹ኢየሱስም መለሰ፥ እንዲህ ሲል:- እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም››፡፡

መንግስተ ሰማይን የሚወርሱት የእግዚአብሐር ልጆች ብቻ ናቸው፡፡ በ1ጴጥሮስ 1፡4 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን በመነሣቱ ለሕያው ተስፋና ለማይጠፋ፥ እድፈትም ለሌለበት፥ ለማያልፍም ርስት እንደ ምሕረቱ ብዛት ሁለተኛ የወለደን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክና አባት ይባረክ፤ ይህም ርስት በመጨረሻው ዘመን ይገለጥ ዘንድ ለተዘጋጀ መዳን በእምነት በእግዚአብሔር ኃይል ለተጠበቃችሁ ለእናንተ በሰማይ ቀርቶላችኋል››፡፡ በክርስቶስ በማመን የእግዚአብሔር ልጅ ሆነዋል? ይህን ካላደረጉ በእግዚአብሔር ቃል መሰረት በሰማይ ርስት የሎትም፡፡

ወድ አንባቢዬ የዘላለም ህይወት እንዳለን እርግጠኛ ነን በሚል ሃሳብ በተከታታይ ከክፍል 1 ጀምሮ እስከዚህኛው ክፍል ድረስ አብራችሁ ስላላችሁ አመሰግናለሁ ቀጣዩን ክፍልም አብረን እንቀጥላለን እስከዚያው ቸር እንሰንብት

ካሱ ቦስተን

የዘላለም ህይወት እንዳለን እርግጠኛ ነን ?

ክፍል 5

ክርስቶስ ቅጣታችንን ተቀብሎልናል !

ሁላችን ኃጢአትን አድርገናል፡፡ እግዚአብሔር ጻድቅ ፈራጅ ስለሆነ ለኃጢአታችን የሚገባንን ፍርድ ልንቀበል ይገባናል፡፡ ይህም ደሞዝ ሞት ነው፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር ፍቅር ስለሆነ ልጁ ኢያሱስ ክርስቶስ ይህንን ቅጣት በእኛ ፈንታ ተቀብሎልናል፡፡ ሮሜ 5፡6-10 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ገና ደካሞች ሳለን ክርስቶስ ዘመኑ ሲደርስ ስለ ኃጢአተኞች ሞቶአልና››፡፡ ይህን ፍቅር ለመረዳት አዳጋች ነው፡፡

በተጨማሪ 1ጴጥሮስ 3፡18 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ክርስቶስ ደግሞ ወደ እግዚአብሔር እንዲያቀርበን እርሱ ጻድቅ ሆኖ ስለ ዓመፀኞች አንድ ጊዜ በኃጢአት ምክንያት ሞቶአልና፤ በሥጋ ሞተ በመንፈስ ግን ሕያው ሆነ››፡፡ ዳግመኛ ወደ እግዚአብሔር እቅፍ እንድንመለስ ጻድቅ የሆነው ክርስቶስ ኃጥኣን በሆነው በእኛ ፈንታ መሰቃየት ነበረበት፡፡ ‹‹እኛ በእርሱ ሆነን የእግዚአብሔር ጽድቅ እንሆን ዘንድ ኃጢአት ያላወቀውን እርሱን ስለ እኛ ኃጢአት አደረገው›› (2ቆሮንቶስ 5፡21)፡፡ ክርስቶስ እኛ ፈጽሞ ልንሰራው የማንችለውን ሥራ ሰርቶልናል፡፡ እዳችንን ከፍሎልናል፡፡ የሰው ልጅ ይህንን እዳ መክፈል ቢችል ኖሮ ክርስቶስ በመስቀል ላይ መሞት ባላስፈለገው ነበር፡፡ በበደላችን ሙታን ነበርን፣ ነገር ግን ከወደደን ከታላቅ ፍቅሩ የተነሳ ክርስቶስ በእኛ ፈንታ እንዲሞት በማድረግ የጽድቅ ፍርዱ ሳይዛባ ከሞት አዳነን፡፡

ሰው የሚድንበት ብቸኛ መንገድ ክርስቶስ ብቻ ነው፡፡ ሌላ ምንም አማራጭ የለንም፡፡ ዮሐንስ 14፡6 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ኢየሱስም፡- እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ፤ በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም››፡፡ ወደ እግዚአብሔር የምንደርስበት መንገድ ክርስቶስ ነው፡፡ በተጨማሪ የሐዋሪያት ሥራ 4፡12 እንዲህ ይላል፡- ‹‹መዳንም በሌላ በማንም የለም፤ እንድንበት ዘንድ የሚገባን ለሰዎች የተሰጠ ስም ከሰማይ በታች ሌላ የለምና››፡፡ በሙሐመድ፣ በቡድሃ፣ በአይሁድንት፣ ወይም በሌሎች በማናቸውም የሃይማኖት ስሞች መዳን የለም፡፡ እኛ በፈጠርነው የክርስትና ሃይማኖት ስርአቶችም ጭምር መዳን የለም፡፡ ድነታችን የምናገኘው እዳችንን በከፈለው በክርስቶስ ብቻ ነው፡፡

እዳችንን ለመክፈል ክርስቶስ ተሰቃይቷል፡፡ የተቀበለውን መከራ ማሰብ አእምሮችን ፈጽሞ አይችልም፡፡ ክርስቶስ ወደዚህ አለም የመጣው በሞቱ እዳችንን ለመክፈል ነው፡፡ የክርስቶስን ሞት የሚተነብዩ በርካታ የብሉይ ኪዳን ጥቅሶች አሉ፡፡ ለአብነት ያህል ክርስቶስ ከመሞቱ ከ700 አመት በፊት የተነገረው የኢሳይያስ ትንቢት አንዱ ነው፡- ‹‹እርሱ ግን ስለ መተላለፋችን ቈሰለ፥ ስለ በደላችንም ደቀቀ፤ የደኅንነታችንም ተግሣጽ በእርሱ ላይ ነበረ፥ በእርሱም ቍስል እኛ ተፈወስን። እኛ ሁላችን እንደ በጎች ተቅበዝብዘን ጠፋን፤ ከእኛ እያንዳንዱ ወደ ገዛ መንገዱ አዘነበለ፤ እግዚአብሔርም የሁላችንን በደል በእርሱ ላይ አኖረ›› (ኢሳይያስ 53፡5-6)፡፡ የክርስቶስ ሞት ድንገተኛ አይደለም፣ የሰውን ልጅ ለመቤዠት የእግዚአብሔር ዘላለማዊ እቅድ እንጂ፡፡

ክርስቶስ ሁሉን በማወቅ ችሎታው ሊሆንበት ያለውን ሁሉ ያውቅ ነበር፡፡ በማቴዎስ 20፡17-19 እንዲህ የሚል ቃል እናነባለን፡- ‹‹ኢየሱስም ወደ ኢየሩሳሌም ሊወጣ ሳለ፥ በመንገድ አሥራ ሁለቱን ደቀ መዛሙርት ብቻቸውን ወደ እርሱ አቅርቦ። እነሆ፥ ወደ ኢየሩሳሌም እንወጣለን፣ የሰው ልጅም ለካህናት አለቆችና ለጻፎች ይሰጣል፤ የሞት ፍርድም ይፈርዱበታል፥ ሊዘባበቱበትም ሊገርፉትም ሊሰቅሉትም ለአሕዛብ አሳልፈው ይሰጡታል፥ በሦስተኛውም ቀን ይነሣል አላቸው››፡፡ ክርስቶስ ያለማንም አስገዳጅነት በፈቃዱ በእኛ ፈንታ ሊሞትልን ወሰነ፡፡

ክርስቶስ በተዋህዶ ሰውም አምላክም ነው፡፡ ሊሆንበት ያለውን ከማወቅ ባሻገር ሥጋ እንደመልበሱ በሞቱ ተጨንቆ ነበር፡፡ ኢየሱስ ከሞቱ ቀን ቀደም ብሎ ባለው ምሽት በጌቴ ሰማኒ የአታክልት ሥፍራ በነበረበት ወቅት የነበረውን ሁኔታ በሉቃስ 22፡41-44 እንዲህ እናነባለን፡- ‹‹ከእነርሱም የድንጋይ ውርወራ የሚያህል ራቀ፥ ተንበርክኮም። አባት ሆይ፥ ብትፈቅድ ይህችን ጽዋ ከእኔ ውሰድ፤ ነገር ግን የእኔ ፈቃድ አይሁን የአንተ እንጂ እያለ ይጸልይ ነበር። ከሰማይም መጥቶ የሚያበረታ መልአክ ታየው። በፍርሃትም ሲጣጣር አጽንቶ ይጸልይ ነበር፤ ወዙም በምድር ላይ እንደሚወርድ እንደ ደም ነጠብጣብ ነበረ››፡፡ ክርስቶስ በእርግጥም በመስቀሉ ምጥ ነው ያዳነን፡፡

በተጨማሪ በ1ጴጥሮስ 2፡24 ላይ የሚከተለውን እናነባለን፡- ‹‹ለኃጢአት ሞተን ለጽድቅ እንድንኖር፥ እርሱ ራሱ በሥጋው ኃጢአታችንን በእንጨት ላይ ተሸከመ››፡፡ በእግዚአብሔር ፊት ጻድቃን ሆነን አንድንታይ ክርስቶስ የኃጢአታችንን እዳ መክፈል ነበረበት፡፡ ሰው በዚህ መንገድ ጻድቅ ሆኖ በእግዚአብሔር ዘንድ ሲታይ እግዚአብሔር ያዘጋጀውን የድነት ስጦታ ተቀብሏልና ከዘላለም ፍርድ ይድናል፡፡

የመስቀል ሞት የሰው ልጅ ሰውን አሰቃይቶ ለመግደል ካበጃቸው የስቃይ ፍርዶች አሰቃቂው ነው፡፡ ከዚህ የባሰ የለም፡፡ ጌታችን በዚህ መስቀል ላይ መግለጽ በሚያስቸግር ስቃይና ጣር ለስድስት ሰአታት ቆየ፡፡ እግዚአብሔር እኛን በማዳን ስራ ውስጥ ጻድቅ ይሆን ዘንድ ቅጣታችንን በመቀበል ስለእኛ ሞተ፡፡ ምን አይነት ፍቅር ነው! እርሶና እኔ ቃሉን ለመታዘዝ ክርስቶስ የከፈለው ዋጋ በቂ ምክኒያታችን አይሆንምን? ስለዚህ የሃጢያታችንን ዋጋ ተቀብሎ የሞተልንን ጌታ አሁን በልባችን አምነን ብንቀበል የዘላለምን ህይወት እናገኛለን። ሌላ ደግሞ ከዚህ ቀጥሎ የእግዚአብሄር ልጅ የመባልን ስልጣን ያገኘንበትም ስለሆነ በቀጣዩ ክፍል እንገናኝ። ቸር እንሰንብት።

ካሱ ቦስተን

የዘላለም ህይወት እንዳለን እርግጠኛ ነን ?

ክፍል 4

የእግዚአብሄር መፍትሄ

ባለፈው ክፍል 3 ላይ የሃጢያት መዘዙን አይተናል በዛሬው ክፍል 4 ላይ  ለሰው ልጆች  የኃጢአት ችግር እግዚአብሔር መፍትሄ ያዘጋጀበትን እውነት እናያለን፡፡ እግዚአብሔር የፍቅር አምላክ ነው፡፡ ዮሐንስ 3፡16፣ ‹‹በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና››፡፡ ነፍስን ለሌላው አሳልፎ ከመስጠት የሚበልጥ ፍቅር ምን ሊሆን ይችላል?

እግዚአብሔር ፍቅር ብቻ ሳይሆን ጻድቅ ፈራጅም ነው፡፡ ዮሐንስ 5፡30፣ ‹‹እኔ ከራሴ አንዳች ላደርግ አይቻለኝም፤ እንደ ሰማሁ እፈርዳለሁ ፍርዴም ቅን ነው፣ የላከኝን ፈቃድ እንጂ ፈቃዴን አልሻምና››፡፡ ፍትህ በኃጥኡ ላይ ይፈርዳል፡፡ ለአብነት የሚከተለውን እንመልከት፡- ባንክ ስዘርፍ ተገኝቼ ለፍርድ ወዳጄ የሆነ ዳኛ ፊት ቀረብኩ እንበል፡፡ ይህ ዳኛ ወደእርሱ ከጠራኝ በኋላ የክስ ወረቀትህን እቀደዋለሁ፤ ከአሁን ጀምሮ ከፍርድ ነጻ ነህ፤ ውጣ፤ ቢለኝ፣ ጻድቅ ፈራጅ ያሰኘዋል? ፈጽሞ! እግዚአብሔር ጻድቅ ፈራጅ ነው፡፡

አግዚአብሔር ሕግ ሰጠ፣ የሰው ልጅ ተላለፈው፣ ፈጣሪም የጽድቅ ፍርድ አስተላለፈ፡፡ ይህም ፍርድ ሞት ይባላል፡፡ የሰው ልጅ በሞት ፍርሃት ውስጥ እየማቀቀ ለበርካታ አመታት በምድር ላይ የስቃይ ኑሮ መግፋት ጀመረ፡፡

ይህን ፍርድ ያስተላለፈው አምላክ ጻድቅ ብቻ ሳይሆን የፍቅር አምላክ በመሆኑ፣ ከእስትንፋሱ የተካፈለው ሰው በምድር ላይ ሲሰቃይ ማየት አላስቻለውም፡፡ በዚህም ምክኒያት ጻድቅ ፈራጅነቱንና የፍቅር አምላክነቱን አዋህዶ የሚያሳይ ሌላ የድነት መንገድ ለሰው ልጅ አዘጋጀ፤ ይህ የድነት መንገድ ጽንፍ የሚመስሉትን የአምላክ ሁለት ባሕሪያት (ፍርድና ምሕረት) በአንድ መስመር ያገናኘ አስገራሚ ክስተት ነበር፡፡ እግዚአብሔር በሰው ዘር ሁሉ ላይ ያሳለፈው ሊታጠፍ የማይችል የሞት ፍርድ ሳይቀለበስ የሰው ልጅ ከተቆጣው አምላኩ ጋር ታረቀ፡፡ የአገራችን የእምነት ሊቃውንት ይህንን ሁኔታ ግሩም በሆነ መንገድ እንዲህ በማለት ይገልጹታል፡፡ “እግዚአብሔር ሰውን ከፈጠረበት ጥበቡ ይልቅ ያዳነበት ጥበቡ ተጠበበች፡፡” የዚህ አስገራሚ ትእይንት ጀማሪና ፈጻሚው ደግሞ ምንም በደል ያልተገኘበት ኢየሱስ ነበር፡፡ እግዚአብሔር በሰው ልጅ ላይ የተቆጣውን ቁጣ በኢየሱስ ላይ አሳረፈው፤ ፍርዱን አሳየ፡፡ ኢየሱስ ስለ ኃጢአተኞቹ ስለ እኛ ሞተ፡፡ በእርሱም ምክኒያት የሰው ልጅ ምኅረትን ተቀበለ፡፡ ከፈጣሪውም የፍርድ ቁጣ ተረፈ ‹‹ይልቁንስ እንግዲህ አሁን በደሙ ከጸደቅን በእርሱ ከቍጣው እንድናለን›› (ሮሜ. 5፡9)፡፡

እግዚአብሔር የፍቅር አምላክ ብቻ ሳይሆን የበቀል አምላክም ጭምር ነው፡፡ ዕብራዊያን 10፡30-31 እነዲህ ይላል፡- ‹‹በቀል የእኔ ነው፣ እኔ ብድራትን እመልሳለሁ ያለውን እናውቃለንና፤ ደግሞም። ጌታ በሕዝቡ ይፈርዳል። በሕያው እግዚአብሔር እጅ መውደቅ የሚያስፈራ ነው››፡፡ ብዙ ሰዎች እግዚአብሔርን በፍቅር አምላክነቱ ብቻ ማወቅ ይሻሉ፡፡ ይህ ግን ስህተት ነው፡፡ በፍርድ ቀን ሁሉ ሰው በእግዚአብሔር እጅ መውደቅ እንዴት ያለ አስፈሪ ነገር እንደሆነ ያውቃሉ፡፡

ኢየሱስ መሞት ለምን አስፈለገው? ምክኒያቱም እግዚአብሔር የፍቅር አምላክ ብቻ ሳይሆን ጻድቅ ፈራጅም ጭምር ስለሆነ፡፡ ፍትህ ከፍርድ ውጪ ሊታሰብ አይችልም፡፡ እግዚአብሔር በመጽሐፍ ቅዱስ የኃጥኡን ኃጢአት እንዴት እነደሚያነጻ ገልጿል፡፡ ለኃጢአታችን መንጻት ይህንን መንገድ ልንከተል ይገባል፡፡ ዛሬም ኩነኔ ያለባቸው ሁሉ ይህን የእግዚአብሔር መንገድ ያልተከተሉቱ ብቻ ናቸው፡፡ እነዚህም ክርስቶስ ዳግም ሲመጣ የሚሆንባቸውን 2ተሰሎንቄ 1፡8-10 እንዲህ በማለት ይገልጽልናል፡- ‹‹እግዚአብሔርን የማያውቁትን፣ ለጌታችንም ለኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል የማይታዘዙትን ይበቀላል፤ በዚያም ቀን በቅዱሳኑ ሊከብር፣ ምስክርነታችንንም አምናችኋልና በሚያምኑት ሁሉ ዘንድ ሊገረም ሲመጣ፥ ከጌታ ፊት ከኃይሉም ክብር ርቀው በዘላለም ጥፋት ይቀጣሉ››፡፡

እግዚአብሔር የጸጋ አምላክም ጭምር ነው፡፡ ጸጋ ለማይገባቸው ሰዎች የተሰጠች የእግዚአብሔር ነጻ ስጦታ ነች፡፡ ሮሜ 3፡23-24 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል››፡፡ ሁላችን ኃጢአትን አድርገናል፡፡ በዚህም ምክኒያት ሁላችን የገሃነም ፍርድ ይገባናል፡፡ ሆኖም ግን እግዚአብሔር በማይገባን ስጦታ (በጸጋ) ማለትም በክርስቶስ ቤዛነት እኛን ሊያድን ወደደ፡፡ ቤዛነታችን ክርስቶስ ነው፡፡ሰው የሚድነው በጸጋው ነው፡፡ በኤፌሶን 2፡8-9 ላይ እንዲህ እናነባለን፡- ‹‹ጸጋው በእምነት አድኖአችኋልና፤ ይህም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው እንጂ ከእናንተ አይደለም፤ ማንም እንዳይመካ ከሥራ አይደለም››፡፡ ‹‹በእምነት መታዘዝ›› (ሮሜ 16፡26) በኩል በጸጋ እንድናለን፡፡ ማንም በመልካምነቱ ወደ መንግስተ ሰማይ የመግባት ድፍረት የለውም፤ ምክኒያቱም ሁሉ ኃጢአትን አድርገዋልና፡፡ በጎነታችን ድነታችንን አይገዛልንም፡፡ ድነታችንን ለማግኘት የሚያስችል ፍጹም ሥራ ልንሰራ አንችልም፡፡ ኢሳይያስ 64፡6 ይመልከቱ፡- ‹‹ሁላችን እንደ ርኩስ ሰው ሆነናል፥ ጽድቃችንም ሁሉ እንደ መርገም ጨርቅ ነው፤ ሁላችንም እንደ ቅጠል ረግፈናል፥ በደላችንም እንደ ነፋስ ወስዶናል››፡፡ በማናችንም ውስጥ ለመዳን የሚሆን ምክኒያት አልተገኘብንም፡፡ ሁላችንን የሚያድነን የተገለጠው የእግዚአብሔር ጸጋ ብቻ ነው፡፡ ይህ የግዚአብሄር ጸጋ እንዴት ነው ያዳነን ? ቀጣዩን በሚቀጥለው ክፍል እናያለን እስከዚያው ቸር እንሰንብት።

ይህንን መልእክት አንብበው ሲጨርሱ ከታች ያለውን ላይክ የሚለውን ከተጫኑ በኋላ ፎሎው የሚለውን ቢነኩ ቀጣዩ ክፍል ሲለቀቅ ወዲያው ያገኛሉ፤ ሃሳብ አስተያየትዎ አይለየኝ፤ ስለሚከታተሉ አመሰግንዎታለሁ።

ካሱ ቦስተን

የዘላለም ህይወት እንዳለን እርግጠኛ ነን ?

ክፍል 3

ኃጢአትና መዘዙ

ባለፈው ክፍል 3 ጽሁፌ ላይ የእግዚአብሄርን የማስጠንቀቂያ ሃሳብ አስፍሬ እንዳነበባችሁት እርግጠኛ ነኝ፤ ካላነበቡት ግን ያንን አንብበው ወደዚህ ክፍል እንዲሻገሩ እጠይቅዎታለሁ። በዛሬው ጽሁፌ ኃጢአት ያመጣብንን መዘዝ እና እንዴት ከእግዚአብሔር እንደለየን እንመለከታለን፡፡ 

ኃጢአት ከእግዚአብሄር እንዴት እንደለየን መጽሃፍ ቅዱስ በኢሳይያስ 59፡2፣ ‹‹ነገር ግን በደላችሁ በእናንተና በአምላካችሁ መካከል ለይታለች፥ እንዳይሰማም ኃጢአታችሁ ፊቱን ከእናንተ ሰውሮታል››፡፡ ብሎ ይነግራናል፤ ከእግዚአብሔር የለየን ኃጢአት ነው፡፡ ሮሜ 3፡23 እንዲህ በማለትም ይህንን ሃሳብ ያጸናልናል ፡- ‹‹ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል››፡፡ በዚህ ምድር ላይ ከኖረ ሰው ኃጢአት ያልሰራ ጌታችን ኢየሱስ ብቻ ነው፡፡ ስለዚህ ሁላችን ድነት ያስፈልገናል፡፡ 1ዮሐንስ 1፡8 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ኃጢአት የለብንም ብንል ራሳችንን እናስታለን፥ እውነትም በእኛ ውስጥ የለም››፡፡ ሰው እራሱን በማሳት የኃጢአት ችግር የለብኝም ሊል ይችላል፡፡ ይህንን ሲል ግን ምን እያለ እንደሆነ 1ዮሐንስ 1፡10 ያሳየናል፡- ‹‹ኃጢአትን አላደረግንም ብንል ሐሰተኛ እናደርገዋለን ቃሉም በእኛ ውስጥ የለም››፡፡ እግዚአብሔር፡- ሁሉ ኃጢአት ሰርተዋል ሲል ሁሉም ሰርተዋል ማለት ነው፤ ያ ማለት እኔ አንተ አንቺ ሁላችንም ማለት ነው፡፡ ኃጢአት ከሰራን ይህ የሰራነው ኃጢአት ያስከተለብን መዘዝ አለ። 

ሮሜ 6፡23 የኃጢአት መዘዝ ምን እንደሆነ ይነግረናል፡- ‹‹የኃጢአት ደመወዝ ሞት ነውና፤ የእግዚአብሔር የጸጋ ስጦታ ግን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን የዘላለም ሕይወት ነው›››፡፡ ሞት መለየት ማለት ነው፡፡ በአካል ስንሞት አካላችን በመቃብር ጉድጓድ ውስጥ ሲቀር ነፍሳችን ግን ወደሰራት አምላክ ትሄዳለች፡፡ የመክብብ መጽሐፍ 12፡7 እንዲህ ይላል፡- ‹‹አፈርም ወደ ነበረበት ምድር ሳይመለስ፥ ነፍስም ወደ ሰጠው ወደ እግዚአብሔር ሳይመለስ ፈጣሪህን አስብ››፡፡ በአካላዊ ሞት ነፍስ ከስጋ ትለያለች፡፡ ይህች ነፍስ ታዲያ ወደፈጣሪዋ ስትመለስ በምድር ላይ በስጋ ውስጥ በነበረችበት ወቅት በሰራችው ኃጢአት ምክኒያት የዘላለም መኖሪያዋን አዘጋጅታ ነውና የመጣችው ወደዚያው ወደዘላለም መኖሪያዋ ትጓዛለች። በክፍል ሁለት ላይ ወደ ዘላለም መኖሪያ የሚያደርሱ ሁለት መንገዶች እንዳሉና አንዱ ወደ ገሃነም (ወደ ዘላለም ሞት) አንዱ ደግሞ ወደ መንግስተ ሰማይ (ወደዘላለም ህይወት) የሚያደርስ እንደሆነ ሁለቱም ደግሞ ወደሚሄዱበት ስፍራ ላይ ለዘላለም እንደሚኖሩ ልዩነቱ ግን አንዱ ገሃነም አንዱ መንግስተ ሰማይ መሆኑን አይተናል። ሲዖል ሁሌም የእሳት ባህር ያለበት ስፍራ እንደሆነና የሁለተኛው ሞት ያገኛቸው ነፍሳት የሚሄዱበትን ስፍራ መጽሃፍ ቅዱስ በራዕይ 20 ላይ ይገልጽልናል።        

በሮሜ 6፡23 ላይ ‹‹የኃጢአት ደመወዝ ሞት ነውና፤ የእግዚአብሔር የጸጋ ስጦታ ግን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን የዘላለም ሕይወት ነው››፡፡ እንደሚል አይተናል፡፡ ይህ ሞት ግን መንፈሳዊ ሞት ነው፡፡ ይህም ለዘላለም ከእግዚአብሔር መለየት ማለት ነው፡፡ ከእግዚአብሔር የተለዩ ሰዎች አድራሻቸው ገሃነም ይባላል፣ ራዕይ 21፡8፡- ‹‹ዳሩ ግን የሚፈሩና የማያምኑ የርኵሳንም የነፍሰ ገዳዮችም የሴሰኛዎችም የአስማተኛዎችም ጣዖትንም የሚያመልኩ የሐሰተኛዎችም ሁሉ ዕድላቸው በዲንና በእሳት በሚቃጠል ባሕር ነው፤ ይኸውም ሁለተኛው ሞት ነው››፡፡ ይህ ሁለተኛ ሞት ለዘላለም ከእግዚአብሔር ተለይቶ መኖር ማለት ነው፡፡

ታዲያ ከዚህ ለዘላለም ከእግዚአብሄር የተለየነውን ወደ እግዚአብሄር እንድንቀርብ መፍትሄው ምንድነው ? ይህንን ጥያቄ ክፍል 4 ላይ እንመለከተዋለን እስከዚያው ቸር እንሰንብት።

ጽሁፉን አንብበው ላይክ የሚለውን ከተጫኑ እና ፎሎው ካደረጉ አዳዲስ ጽሁፎች ሲለጠፉ ወዲያውኑ ያገኛሉ፤ ለሌሎችም ማካፈል አይርሱ። 

ሃሳብ አስተያየት እንዲሁም ጥያቄ ካለዎት በአስተያየት መስጫው ላይ ያስፍሩ አመሰግናለሁ። 

ካሱ ቦስተን