የዘላለም ህይወት እንዳለን እርግጠኛ ነን ?

ክፍል 4

የእግዚአብሄር መፍትሄ

ባለፈው ክፍል 3 ላይ የሃጢያት መዘዙን አይተናል በዛሬው ክፍል 4 ላይ  ለሰው ልጆች  የኃጢአት ችግር እግዚአብሔር መፍትሄ ያዘጋጀበትን እውነት እናያለን፡፡ እግዚአብሔር የፍቅር አምላክ ነው፡፡ ዮሐንስ 3፡16፣ ‹‹በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና››፡፡ ነፍስን ለሌላው አሳልፎ ከመስጠት የሚበልጥ ፍቅር ምን ሊሆን ይችላል?

እግዚአብሔር ፍቅር ብቻ ሳይሆን ጻድቅ ፈራጅም ነው፡፡ ዮሐንስ 5፡30፣ ‹‹እኔ ከራሴ አንዳች ላደርግ አይቻለኝም፤ እንደ ሰማሁ እፈርዳለሁ ፍርዴም ቅን ነው፣ የላከኝን ፈቃድ እንጂ ፈቃዴን አልሻምና››፡፡ ፍትህ በኃጥኡ ላይ ይፈርዳል፡፡ ለአብነት የሚከተለውን እንመልከት፡- ባንክ ስዘርፍ ተገኝቼ ለፍርድ ወዳጄ የሆነ ዳኛ ፊት ቀረብኩ እንበል፡፡ ይህ ዳኛ ወደእርሱ ከጠራኝ በኋላ የክስ ወረቀትህን እቀደዋለሁ፤ ከአሁን ጀምሮ ከፍርድ ነጻ ነህ፤ ውጣ፤ ቢለኝ፣ ጻድቅ ፈራጅ ያሰኘዋል? ፈጽሞ! እግዚአብሔር ጻድቅ ፈራጅ ነው፡፡

አግዚአብሔር ሕግ ሰጠ፣ የሰው ልጅ ተላለፈው፣ ፈጣሪም የጽድቅ ፍርድ አስተላለፈ፡፡ ይህም ፍርድ ሞት ይባላል፡፡ የሰው ልጅ በሞት ፍርሃት ውስጥ እየማቀቀ ለበርካታ አመታት በምድር ላይ የስቃይ ኑሮ መግፋት ጀመረ፡፡

ይህን ፍርድ ያስተላለፈው አምላክ ጻድቅ ብቻ ሳይሆን የፍቅር አምላክ በመሆኑ፣ ከእስትንፋሱ የተካፈለው ሰው በምድር ላይ ሲሰቃይ ማየት አላስቻለውም፡፡ በዚህም ምክኒያት ጻድቅ ፈራጅነቱንና የፍቅር አምላክነቱን አዋህዶ የሚያሳይ ሌላ የድነት መንገድ ለሰው ልጅ አዘጋጀ፤ ይህ የድነት መንገድ ጽንፍ የሚመስሉትን የአምላክ ሁለት ባሕሪያት (ፍርድና ምሕረት) በአንድ መስመር ያገናኘ አስገራሚ ክስተት ነበር፡፡ እግዚአብሔር በሰው ዘር ሁሉ ላይ ያሳለፈው ሊታጠፍ የማይችል የሞት ፍርድ ሳይቀለበስ የሰው ልጅ ከተቆጣው አምላኩ ጋር ታረቀ፡፡ የአገራችን የእምነት ሊቃውንት ይህንን ሁኔታ ግሩም በሆነ መንገድ እንዲህ በማለት ይገልጹታል፡፡ “እግዚአብሔር ሰውን ከፈጠረበት ጥበቡ ይልቅ ያዳነበት ጥበቡ ተጠበበች፡፡” የዚህ አስገራሚ ትእይንት ጀማሪና ፈጻሚው ደግሞ ምንም በደል ያልተገኘበት ኢየሱስ ነበር፡፡ እግዚአብሔር በሰው ልጅ ላይ የተቆጣውን ቁጣ በኢየሱስ ላይ አሳረፈው፤ ፍርዱን አሳየ፡፡ ኢየሱስ ስለ ኃጢአተኞቹ ስለ እኛ ሞተ፡፡ በእርሱም ምክኒያት የሰው ልጅ ምኅረትን ተቀበለ፡፡ ከፈጣሪውም የፍርድ ቁጣ ተረፈ ‹‹ይልቁንስ እንግዲህ አሁን በደሙ ከጸደቅን በእርሱ ከቍጣው እንድናለን›› (ሮሜ. 5፡9)፡፡

እግዚአብሔር የፍቅር አምላክ ብቻ ሳይሆን የበቀል አምላክም ጭምር ነው፡፡ ዕብራዊያን 10፡30-31 እነዲህ ይላል፡- ‹‹በቀል የእኔ ነው፣ እኔ ብድራትን እመልሳለሁ ያለውን እናውቃለንና፤ ደግሞም። ጌታ በሕዝቡ ይፈርዳል። በሕያው እግዚአብሔር እጅ መውደቅ የሚያስፈራ ነው››፡፡ ብዙ ሰዎች እግዚአብሔርን በፍቅር አምላክነቱ ብቻ ማወቅ ይሻሉ፡፡ ይህ ግን ስህተት ነው፡፡ በፍርድ ቀን ሁሉ ሰው በእግዚአብሔር እጅ መውደቅ እንዴት ያለ አስፈሪ ነገር እንደሆነ ያውቃሉ፡፡

ኢየሱስ መሞት ለምን አስፈለገው? ምክኒያቱም እግዚአብሔር የፍቅር አምላክ ብቻ ሳይሆን ጻድቅ ፈራጅም ጭምር ስለሆነ፡፡ ፍትህ ከፍርድ ውጪ ሊታሰብ አይችልም፡፡ እግዚአብሔር በመጽሐፍ ቅዱስ የኃጥኡን ኃጢአት እንዴት እነደሚያነጻ ገልጿል፡፡ ለኃጢአታችን መንጻት ይህንን መንገድ ልንከተል ይገባል፡፡ ዛሬም ኩነኔ ያለባቸው ሁሉ ይህን የእግዚአብሔር መንገድ ያልተከተሉቱ ብቻ ናቸው፡፡ እነዚህም ክርስቶስ ዳግም ሲመጣ የሚሆንባቸውን 2ተሰሎንቄ 1፡8-10 እንዲህ በማለት ይገልጽልናል፡- ‹‹እግዚአብሔርን የማያውቁትን፣ ለጌታችንም ለኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል የማይታዘዙትን ይበቀላል፤ በዚያም ቀን በቅዱሳኑ ሊከብር፣ ምስክርነታችንንም አምናችኋልና በሚያምኑት ሁሉ ዘንድ ሊገረም ሲመጣ፥ ከጌታ ፊት ከኃይሉም ክብር ርቀው በዘላለም ጥፋት ይቀጣሉ››፡፡

እግዚአብሔር የጸጋ አምላክም ጭምር ነው፡፡ ጸጋ ለማይገባቸው ሰዎች የተሰጠች የእግዚአብሔር ነጻ ስጦታ ነች፡፡ ሮሜ 3፡23-24 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል››፡፡ ሁላችን ኃጢአትን አድርገናል፡፡ በዚህም ምክኒያት ሁላችን የገሃነም ፍርድ ይገባናል፡፡ ሆኖም ግን እግዚአብሔር በማይገባን ስጦታ (በጸጋ) ማለትም በክርስቶስ ቤዛነት እኛን ሊያድን ወደደ፡፡ ቤዛነታችን ክርስቶስ ነው፡፡ሰው የሚድነው በጸጋው ነው፡፡ በኤፌሶን 2፡8-9 ላይ እንዲህ እናነባለን፡- ‹‹ጸጋው በእምነት አድኖአችኋልና፤ ይህም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው እንጂ ከእናንተ አይደለም፤ ማንም እንዳይመካ ከሥራ አይደለም››፡፡ ‹‹በእምነት መታዘዝ›› (ሮሜ 16፡26) በኩል በጸጋ እንድናለን፡፡ ማንም በመልካምነቱ ወደ መንግስተ ሰማይ የመግባት ድፍረት የለውም፤ ምክኒያቱም ሁሉ ኃጢአትን አድርገዋልና፡፡ በጎነታችን ድነታችንን አይገዛልንም፡፡ ድነታችንን ለማግኘት የሚያስችል ፍጹም ሥራ ልንሰራ አንችልም፡፡ ኢሳይያስ 64፡6 ይመልከቱ፡- ‹‹ሁላችን እንደ ርኩስ ሰው ሆነናል፥ ጽድቃችንም ሁሉ እንደ መርገም ጨርቅ ነው፤ ሁላችንም እንደ ቅጠል ረግፈናል፥ በደላችንም እንደ ነፋስ ወስዶናል››፡፡ በማናችንም ውስጥ ለመዳን የሚሆን ምክኒያት አልተገኘብንም፡፡ ሁላችንን የሚያድነን የተገለጠው የእግዚአብሔር ጸጋ ብቻ ነው፡፡ ይህ የግዚአብሄር ጸጋ እንዴት ነው ያዳነን ? ቀጣዩን በሚቀጥለው ክፍል እናያለን እስከዚያው ቸር እንሰንብት።

ይህንን መልእክት አንብበው ሲጨርሱ ከታች ያለውን ላይክ የሚለውን ከተጫኑ በኋላ ፎሎው የሚለውን ቢነኩ ቀጣዩ ክፍል ሲለቀቅ ወዲያው ያገኛሉ፤ ሃሳብ አስተያየትዎ አይለየኝ፤ ስለሚከታተሉ አመሰግንዎታለሁ።

ካሱ ቦስተን

የዘላለም ህይወት እንዳለን እርግጠኛ ነን ?

ክፍል 3

ኃጢአትና መዘዙ

ባለፈው ክፍል 3 ጽሁፌ ላይ የእግዚአብሄርን የማስጠንቀቂያ ሃሳብ አስፍሬ እንዳነበባችሁት እርግጠኛ ነኝ፤ ካላነበቡት ግን ያንን አንብበው ወደዚህ ክፍል እንዲሻገሩ እጠይቅዎታለሁ። በዛሬው ጽሁፌ ኃጢአት ያመጣብንን መዘዝ እና እንዴት ከእግዚአብሔር እንደለየን እንመለከታለን፡፡ 

ኃጢአት ከእግዚአብሄር እንዴት እንደለየን መጽሃፍ ቅዱስ በኢሳይያስ 59፡2፣ ‹‹ነገር ግን በደላችሁ በእናንተና በአምላካችሁ መካከል ለይታለች፥ እንዳይሰማም ኃጢአታችሁ ፊቱን ከእናንተ ሰውሮታል››፡፡ ብሎ ይነግራናል፤ ከእግዚአብሔር የለየን ኃጢአት ነው፡፡ ሮሜ 3፡23 እንዲህ በማለትም ይህንን ሃሳብ ያጸናልናል ፡- ‹‹ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል››፡፡ በዚህ ምድር ላይ ከኖረ ሰው ኃጢአት ያልሰራ ጌታችን ኢየሱስ ብቻ ነው፡፡ ስለዚህ ሁላችን ድነት ያስፈልገናል፡፡ 1ዮሐንስ 1፡8 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ኃጢአት የለብንም ብንል ራሳችንን እናስታለን፥ እውነትም በእኛ ውስጥ የለም››፡፡ ሰው እራሱን በማሳት የኃጢአት ችግር የለብኝም ሊል ይችላል፡፡ ይህንን ሲል ግን ምን እያለ እንደሆነ 1ዮሐንስ 1፡10 ያሳየናል፡- ‹‹ኃጢአትን አላደረግንም ብንል ሐሰተኛ እናደርገዋለን ቃሉም በእኛ ውስጥ የለም››፡፡ እግዚአብሔር፡- ሁሉ ኃጢአት ሰርተዋል ሲል ሁሉም ሰርተዋል ማለት ነው፤ ያ ማለት እኔ አንተ አንቺ ሁላችንም ማለት ነው፡፡ ኃጢአት ከሰራን ይህ የሰራነው ኃጢአት ያስከተለብን መዘዝ አለ። 

ሮሜ 6፡23 የኃጢአት መዘዝ ምን እንደሆነ ይነግረናል፡- ‹‹የኃጢአት ደመወዝ ሞት ነውና፤ የእግዚአብሔር የጸጋ ስጦታ ግን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን የዘላለም ሕይወት ነው›››፡፡ ሞት መለየት ማለት ነው፡፡ በአካል ስንሞት አካላችን በመቃብር ጉድጓድ ውስጥ ሲቀር ነፍሳችን ግን ወደሰራት አምላክ ትሄዳለች፡፡ የመክብብ መጽሐፍ 12፡7 እንዲህ ይላል፡- ‹‹አፈርም ወደ ነበረበት ምድር ሳይመለስ፥ ነፍስም ወደ ሰጠው ወደ እግዚአብሔር ሳይመለስ ፈጣሪህን አስብ››፡፡ በአካላዊ ሞት ነፍስ ከስጋ ትለያለች፡፡ ይህች ነፍስ ታዲያ ወደፈጣሪዋ ስትመለስ በምድር ላይ በስጋ ውስጥ በነበረችበት ወቅት በሰራችው ኃጢአት ምክኒያት የዘላለም መኖሪያዋን አዘጋጅታ ነውና የመጣችው ወደዚያው ወደዘላለም መኖሪያዋ ትጓዛለች። በክፍል ሁለት ላይ ወደ ዘላለም መኖሪያ የሚያደርሱ ሁለት መንገዶች እንዳሉና አንዱ ወደ ገሃነም (ወደ ዘላለም ሞት) አንዱ ደግሞ ወደ መንግስተ ሰማይ (ወደዘላለም ህይወት) የሚያደርስ እንደሆነ ሁለቱም ደግሞ ወደሚሄዱበት ስፍራ ላይ ለዘላለም እንደሚኖሩ ልዩነቱ ግን አንዱ ገሃነም አንዱ መንግስተ ሰማይ መሆኑን አይተናል። ሲዖል ሁሌም የእሳት ባህር ያለበት ስፍራ እንደሆነና የሁለተኛው ሞት ያገኛቸው ነፍሳት የሚሄዱበትን ስፍራ መጽሃፍ ቅዱስ በራዕይ 20 ላይ ይገልጽልናል።        

በሮሜ 6፡23 ላይ ‹‹የኃጢአት ደመወዝ ሞት ነውና፤ የእግዚአብሔር የጸጋ ስጦታ ግን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን የዘላለም ሕይወት ነው››፡፡ እንደሚል አይተናል፡፡ ይህ ሞት ግን መንፈሳዊ ሞት ነው፡፡ ይህም ለዘላለም ከእግዚአብሔር መለየት ማለት ነው፡፡ ከእግዚአብሔር የተለዩ ሰዎች አድራሻቸው ገሃነም ይባላል፣ ራዕይ 21፡8፡- ‹‹ዳሩ ግን የሚፈሩና የማያምኑ የርኵሳንም የነፍሰ ገዳዮችም የሴሰኛዎችም የአስማተኛዎችም ጣዖትንም የሚያመልኩ የሐሰተኛዎችም ሁሉ ዕድላቸው በዲንና በእሳት በሚቃጠል ባሕር ነው፤ ይኸውም ሁለተኛው ሞት ነው››፡፡ ይህ ሁለተኛ ሞት ለዘላለም ከእግዚአብሔር ተለይቶ መኖር ማለት ነው፡፡

ታዲያ ከዚህ ለዘላለም ከእግዚአብሄር የተለየነውን ወደ እግዚአብሄር እንድንቀርብ መፍትሄው ምንድነው ? ይህንን ጥያቄ ክፍል 4 ላይ እንመለከተዋለን እስከዚያው ቸር እንሰንብት።

ጽሁፉን አንብበው ላይክ የሚለውን ከተጫኑ እና ፎሎው ካደረጉ አዳዲስ ጽሁፎች ሲለጠፉ ወዲያውኑ ያገኛሉ፤ ለሌሎችም ማካፈል አይርሱ። 

ሃሳብ አስተያየት እንዲሁም ጥያቄ ካለዎት በአስተያየት መስጫው ላይ ያስፍሩ አመሰግናለሁ። 

ካሱ ቦስተን

የዘላለም ሕይወት እንዳለን እርግጠኛ ነን ?

ክፍል 2

የእግዚአብሔር ማስጠንቀቂያ !

የዘላለም ህይወት እንዳለን እርግጠኛ ነን ? በሚለው ርዕስ ስር 10 ክፍሎች ያሉትን የመጀመሪያውን ክፍል 1 ን አግኝተው እንዳነበቡ እርግጠኛ ነኝ ካላነበብቡት ግን ይህንን ጽሁፍ ከማንበብዎ አስቀድመው የክፍል 1 ሃሳብን አንብበው ይህንን ክፍል 2 ን እንዲቀጥሉ ከአደራ ጋር እጠይቅዎታለሁ። በዛሬው ጽሁፌ ላይ የእግዚአብሄር ማስጠንቀቂያ የሆነውን ሃሳብ ከመጽሃፍ ቅዱሳችን ላይ እንመልከት፦

ሁሉን የሚያውቅ አምላካችን ክርስቶስ በፍርድ ቀን ብዙዎች እንደሚጠፉና ጥቂቶች ብቻ እንደሚድኑ አስረግጦ ነግሮናል፡፡ ማቴዎስ 7፡13-14 እንዲህ ይላል፡- ‹በጠበበው ደጅ ግቡ፤ ወደ ጥፋት የሚወስደው ደጅ ሰፊ፣ መንገዱም ትልቅ ነውና ወደ እርሱም የሚገቡ ብዙዎች ናቸው›፡፡ ይህ ጉዳይ ትኩረታችንን ሊስብ የሚገባ ነገር ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ መሰረት በርካቶቹ የአለማችን ሕዝቦች መንግስተ ሰማይን አይወርሱም፡፡ እነዚህ ሰዎች በሰፊው ጎዳና ወደዘላለም ጥፋት የሚሄዱ ናቸው፡፡ ይህንን ማስጠንቀቂያ ያለማመቻመች ልንቀበለው ይገባል፡፡ ጌታ ኢየሱስ እንዳለው የሚድኑት ጥቂቶች ናቸው፡፡

ለመሆኑ ጥቂት ሲባል ምን ያህል ነው? በ 1ጴጥሮስ 3፡20 ላይ እንዲህ ተጽፏል፡- ‹‹ጥቂቶች ማለት ስምንት ነፍስ በውኃ የዳኑበት መርከብ ሲዘጋጅ፣ የእግዚአብሔር ትዕግሥት በኖኅ ዘመን በቈየ ጊዜ ቀድሞ አልታዘዙም››፡፡ በኖኅ ዘመን ምድራችን ላይ እስከ ሁለት መቶ ሚሊዮን ሰዎች ይኖሩ እንደነበር ይገመታል፡፡ ነገር ግን ከእነዚህ ሰዎች መካከል ከጥፋት ውሃ መትረፍ የቻሉት ስምንት ሰዎች ብቻ ነበሩ፡፡ይህ አስደሳች ቁጥር አይደለም፡፡ ምንም እንኳን መጽሐፍ ቅዱስ በ 2ጴጥሮስ 3፡9 ላይ ‹‹ለአንዳንዶች የሚዘገይ እንደሚመስላቸው ጌታ ስለ ተስፋ ቃሉ አይዘገይም፣ ነገር ግን ሁሉ ወደ ንስሐ እንዲደርሱ እንጂ ማንም እንዳይጠፋ ወዶ ስለ እናንተ ይታገሣል›› ቢልም፣ ጌታ ኢየሱስ በማቴዎስ 7፡13-14 ላይ ስለዘላለም ሕይወት ሲናገር ድነት የሚያገኙት ጥቂቶች ብቻ እንደሆኑ ይናገራል ‹‹በጠበበው ደጅ ግቡ፤ ወደ ጥፋት የሚወስደው ደጅ ሰፊ፥ መንገዱም ትልቅ ነውና፥ ወደ እርሱም የሚገቡ ብዙዎች ናቸው››፡፡ የተቀሩት በርካታዎቹ፣ የዘላለም ሕይወታቸውን እሳቱ በማይጠፋበት ገሀነም ያጠፋሉ፡፡

ወደ ዘላለም ሕይወት የሚያደርሱ ሁለት መንገዶች አሉ፡፡ ከእነዚህ መካከል አንዱ ብቻ ወደ መንግስተ ሰማይ ያደርሰናል፡፡ እኛ የሰው ልጆች በአሁኑ ሰአት ከሁለቱ በአንዱ መንገድ ላይ እንገኛለን፡፡ አንድ ነገር ልጠይቅዎትና እርሶ በየትኛው መንገድ ላይ እንዳሉ ያውቃሉ? ምርጫው የእርሶ ነው፡፡ ነጻ ፈቃድ አሎት፡፡ ከእንስሳት ከሚለይዎት ነገሮች መካከል አንዱ ይህ ነጻ ፈቃድዎ ነው፡፡

እግዚአብሔር ማንም እንዳይጠፋ የሚፈልግ ቢሆንም፣ ምርጫውን ግን ለእኛ ሰጥቷል፡፡ 2ጴጥሮስ 3፡9 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ለአንዳንዶች የሚዘገይ እንደሚመስላቸው ጌታ ስለ ተስፋ ቃሉ አይዘገይም፥ ነገር ግን ሁሉ ወደ ንስሐ እንዲደርሱ እንጂ ማንም እንዳይጠፋ ወዶ ስለ እናንተ ይታገሣል››፡፡  1ጢሞቴዎስ 2፡4 ስለ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሰዎች ሁሉ ሊድኑና እውነቱን ወደ ማወቅ ሊደርሱ በሚወድ በእግዚአብሔር በመድኃኒታችን ፊት መልካምና ደስ የሚያሰኝ ይህ ነው››፡፡ እንግዳው ለመዳን በእጃችን ላይ ያለውን ውሳኔ እንጠቀም፡፡ድነትን ለማግኘት ስለ ድነት ትክክለኛ እውቀት ሊኖረን ይገባል፡፡ ኢየሱስ እንዲህ አለ፡- ‹‹እውነትንም ታውቃላችሁ እውነትም አርነት ያወጣችኋል አላቸው› የዮሐንስ ወንጌል 8፡32፡፡ ለመሆኑ አርነት የሚያወጣን እውነት ምንድን ነው? በዮሐንስ ወንጌል 17፡17 ላይ እንዲህ የሚል ቃል ሰፍሮ እናገኛለን፡- ‹‹በእውነትህ ቀድሳቸው፤ ቃልህ እውነት ነው››፡፡ ስለዚህ ወደ መንግስተ ሰማይ እንድንገባ አርነት የሚያወጣን እውነት ያለው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ብቻ ነው፡፡መቼም በቤትዎ መጽሃፍ ቅዱስ እንዳለና እያነበቡት እንዳለ እርግጠኛ ነኝ። ስለዚህ መጽሃፍ ቅዱስ ውስጥ ኃጢአት ምን እንደሆነና መዘዙን ሁሉ አስፍሮልናል። በሚቀጥለው ክፍል 3 ጽሁፌ ላይ ኃጢአት የሚያመጣቸውን መዘዞች ይዤልዎት እመጣለሁ እስከዚያው ሰላም ቆዩኝ፡፡

ይህንን ጽሁፍ ካነበቡ በኋላ ለአንድ ወዳጅዎ ማካፈልዎትን አይርሱ አስተያየትና ጥያቄ ካለዎት በሃሳብ መስጫው ላይ ያስፍሩ፤ አመሰግንዎታለሁ።

ካሱ ቦስተን

የዘላለም ሕይወት እንዳለን እርግጠኛ ነን ?

ክፍል 1

የዘላለም ሕይወታችን

“የዘላለም ሕይወት እንዳለን እርግጠኛ ነን?” የሚለው ይህ ጽሁፍ 10 ክፍሎች አሉት፡፡ ለዛሬው ክፍል 1 ን ይዤ ቀርቤያለሁ፤ ማንኛውም ጥያቄ ሆነ አስተያየት ቢኖርዎ፣ በአስተያየት መስጫው ላይ ቢያሰፍሩ ተገቢውን ምላሽ ለመስጠት ቃል እገባለሁ፡፡

በዚህ ጽሁፍ ውስጥ የቀረቡ ሃሳቦች የእኔን አስተሳሰብና ግምት የያዙ ሳይሆኑ በቀጥታ መጽሐፍ ቅዱስ የሚለውን የሚናገሩ ናቸው፡፡ መጽሐፍ ቅዱሱ ሲናገር ልንናገር፣ ዝም ሲል ደግሞ ዝም ልንል ግድ ነውና፡፡ የምናደርጋቸውን ነገሮች ሁሉ በመጽሐፍ ቅዱስ መሰረት ልናደርጋቸው፣ በጽሐፉ በስማቸው የሚጠራቸውንም በግልጽ ልንጠራቸው ይገባል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ከሚለው ያነሰ፣ የበዛ፣ ወይም የተለየ ነገር ሁሉ የስህተት ትምህርት ነውና፡፡

ከእግዚአብሔር ቃል እውቀት ማነስ የተነሳ በተፈጠሩት በርካታ ሃይማኖቶች ምክኒያት በአለም ሕዝቦች መካከል ከፍተኛ ግራ በጋባት ይስተዋላል፡፡ በአሁኑ ሰአት በአለማችን ላይ የተለያየ አስተምህሮዎች፣ የስነ መለኮት ምልከታዎች እና አስተሳሰቦች ያልዋቸው ከ 600 በላይ ቤተ እምነቶች ይገኛሉ፡፡ በእነዚህ በርካታ እምነቶች ‹የእመን› ጥያቄ የሚቀርብላቸው የአለማችን ሰዎች ምን እና ማንን ማመን እንዳለባቸው ለመወሰን ግራ ተጋብተዋል፡፡ አዳኛችን የሆነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ በፈቃዱ በከፈለው ስቃይና ሞት ለኃጢአታችን ይቅርታ የሚያስፈልገውን ሁሉ አቅርቦልናል፡፡ በፍርድ ቀን ከሰይጣንና ከመላእክቱ ጋር ወደ ወደ ዘላለም እቶን እሳት መጣል አይገባንም፡፡ እናም ለመዳን የወንጌልን እውነት መታዘዝ ይኖርብናል፡፡ ወንጌል ምንድን ነው? ለመዳን ምን ማድረግ ይኖርብናል? በዚህ ጽሁፍ ውስጥ እግዚአብሔር በሰማይ ያዘጋጀልንን የዘላለም ሕይወት ስጦታ ለመውረስ መጽሐፍ ቅዱስ ምን ማድረግ እንዳለብን የሚናገረውን አብረን እናነባለን፡፡

ከመጽሐፍ ቅዱስ የተወሰዱ ጥቅሶች በሙሉ ጠመም/ዘመም ባለ የፊደል አጻጻፍና ደማቅ ሆነው የቀረቡ ሲሆን ለእነዚህ ጥቅሶች ልብዎንና አእምሮዎን ሊከፍቱ ይገባል፡፡ እግዚአብሔር በእነዚህ ቃሎች ውስጥ ምን ሊያስተላልፍ እንደፈለገ መግለጥ የዚህ ጽሁፍ ዋነኛ አላማ ነው፡፡ ከመጽሐፍ ቅዱስ የተወሰዱትን እነዚህን ጥቅሶችን ሲያነቡ ለተሰመረባቸው ቃላት ልዩ ትኩረት እንዲሰጡ እጠይቅዎታለሁ፡፡

የዘላለም ሕይወት ስለማግኘትዎ እርግጠኛ ነዎት? ይህ ጥያቄ የዘላለም ሕይወትን በተመለከተ ዋነኛ ጥያቄያችን መሆን አለበት፡፡ ዛሬ ብንሞት በእርግጠኝነት በቀጥታ ወደ ገነት እንደምንሄድ እናውቃለን? ነፍሳችን ከስጋችን ከተለየች በኋላ ይህን የምርጫ እድል ዳግመኛ የማናገኝበት በመሆኑ ጥያቄውን በቸልታ ልናልፈው አይገባም፡፡ አንድ ቀን፣ ለዚህ ጥያቄ የሰጠነውን ምላሽ ለማወቅ ሁላችን በፍርድ ወንበር ፊት እንቀርባለን፡፡ የሰው ልጅ ሊያስቀራቸው የማይችላቸው ሁለት ነገሮች ከፊቱ ይጠብቁታል፡፡ እነዚህ ነገሮች ሞትና ፍርድ ይሰኛሉ፡፡ ‹‹ለሰዎችም አንድ ጊዜ መሞት ከእርሱ በኋላም ፍርድ እንደ ተመደበባቸው፣›› ዕብራዊያን 9፡27፡፡ ማንም ሰው እነዚህን ነገሮች ሊያመልጥ አይችልም፡፡

ማንም ሰው ስለነገው ቀርቶ ከጥቂት ሰከንዶች በኋላ ስለሚሆነው ነገር እርግጠኛ ሊሆን አይችልም፡፡ ስለዚህ በምንም መንገድ ይህን ጥያቄ ለነገ ልንገፋው አይገባንም፡፡ እግዚአብሔር በያዕቆብ መልእክት 4፡14 ላይ እንዲህ ሲል ያስጠነቅቀናል፡- ‹‹…ነገ የሚሆነውን አታውቁምና። ሕይወታችሁ ምንድር ነው? ጥቂት ጊዜ ታይቶ ኋላ እንደሚጠፋ እንፍዋለት ናችሁና።››

ለእኛ አእምሮ ‹‹ትክክል›› እና ‹‹ስህተት›› በሚመስሉን መመዘኛዎች ላይ ተመስርተን የዘላለም ሕይወትን በሚያህል ውድ ነገር ላይ ስህተት መስራት የለብንም፡፡ ለዚህ ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት በስሜቶቻችንም ላይ ቢሆን መመስረት የለብንም፡፡ እስቲ መጽሐፍ ቅዱስ በምሳሌ 14፡12 ላይ የሚለውን እንመልከት፡- ‹‹ለሰው ቅን የምትመስል መንገድ አለች ፍጻሜዋ ግን የሞት መንገድ ነው››፡፡ ለውሳኔዎቻችን ትክክለኛነት ማረጋገጫው መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ መሆን ይገባዋል፡፡

ደኅንነታችንን (ድነታችንን) በተመለከተ የግል ግምቶቻችን ምንድን ናቸው? እኛ የምናቀርባቸው ብዙዎቹ ግምቶች እግዚአብሔር በቃሉ ካስቀመጠው እውነታ ጋር የሚቃረኑ ናቸው፡፡ ስለዚህ ያሉንን ግምቶች ሁሉ በእግዚአብሔር ቃል መፈተሸ ይኖርብናል፡፡ ይህንን በምናደርግበት ወቅት በእኛና በእግዚአብሔር ቃል መካከል ያሉ በርካታ ልዩነቶችን ማስተዋል እንጀምራለን፡፡ ጌታችን በማርቆስ 7፡7 እንዲህ ይላል፡- ‹‹የሰውም ሥርዓት የሆነ ትምህርት እያስተማሩ በከንቱ ያመልኩኛል ተብሎ እንደ ተጻፈ በእውነት ትንቢት ተናገረ››፡፡ አምልኮአችን በእግዚአብሔር ቃል ላይ ያልተመሰረተ ሲሆን ከንቱ ይሆናል። የእነዚህ ሁሉ አደናጋሪ ትምህርቶች ምንጭ እግዚአብሔር ይመስሎታል? ፈጽሞ! 1ቆሮንቶስ 14፡33 እንዲህ ይላል፡- ‹‹እግዚአብሔርስ የሰላም አምላክ ነው እንጂ የሁከት አምላክ አይደለምና፤ በቅዱሳንም አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ እንዲህ ነው››፡፡ ሐዋሪያው ጴጥሮስ ለአይሁድ ሸንጎ በሐዋሪያት ሥራ 5፡29 ላይ እንዲህ ብሎ ተናገረ፡- ‹‹ከሰው ይልቅ ለእግዚአብሔር ልንታዘዝ ይገባል››፡፡

በመጨረሻው ዘመን የሰውም ሆነ የእኛ አስተያየት ከፍርድ ለማምለጥ ምክኒያት አይሆኑንም፡፡ ከፍርድ የሚያስመልጠን በእግዚአብሔር ቃል መሰረት ያመነው ነገር ብቻ ነው፡፡ ጌታ ኢየሱስ፣ ስለ ዘላለም ሕይወት አስመልክቶ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ በነገረን እውነት አንጻር የምንዳኝበት የፍርድ ቀን ይመጣል፡፡ ፍርድ የሚሰጠው በዚህ መመዘኛ ብቻ ነው፤ ምክኒያቱም ጌታችንና መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲህ ብሎ ተናግሯልና፣ የዮሐንስ ወንጌል 12፡48 ‹‹በማይቀበለኝና ቃሌን በሚያቃልል ላይ የሚፈርድበት አለ፤ የተናገርሁት ቃል ራሱ በመጨረሻው ቀን ይፈርድበታል››፡፡ (ከአዲሱ መደበኛ ትርጉም መ/ቅ የተወሰደ) ስለዚህ የዘላለም ሕይወትን አስመልክቶ ማንም ሰው የመጽሐፍ ቅዱስ ማስረጃ በሌለበት የግሉን አስተያየት ቢሰጠን ልንቃወም ይገባል፡፡ ከነፍሳችን በላይ ምን ሊያሳስበን የሚችል ነገር ይኖራል?

የነፍሳችንን ዋጋ በአለም ያለ ምንም ነገር ሊመጥነው እንደማይችል ያውቃሉ? ማቴዎስ 16፡26 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሰው ዓለምን ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱን ግን ቢያጣ ምን ይጠቅመዋል? ወይስ ሰው በነፍሱ ምትክ ሊከፍለው የሚችለው ዋጋ ምንድነው?›› (ከአዲሱ መደበኛ ትርጉም መ/ቅ የተወሰደ) ነፍሳችን ዘላለማዊ ናት፡፡ እናም ይህችን ነፍስ ለዘላለም በእቶን እሳት ውስጥ እንድትኖር ሊያደርጋት የሚችሉ ጉዳዮችን ሁሉ በቸልታ መመልከት ፈጽሞ አይገባንም፡፡

ክፍል 2 ን በሚቀጥለው ጽሁፌ ይዤልዎት እቀርባለሁ እስከዚያው ቸር እንሰንብት።

ካሱ ቦስተን

መንፈሳዊ ትረካ

የመጨረሻው ትንቅንቅ ቁጥር 2 መንፈሳዊ ትረካ የሚቀጥለው ቅዳሜ በ 2/19/22 ማለዳ ይቀርብላችኋል ቁጥር አንድ ትረካን “kassuboston” ብለው በስልክዎም ሆነ በኮምፒውተር ላይ ጎግል በማድረግ ዩቲዩብ ላይ ገብተው ማዳመጥ ይችላሉ አመሰግናለሁ
ካሱ ቦስተን

ጋብቻ

መጋባት በሁሉ ዘንድ ክቡር መኝታውም ንጹሕ ይሁን፤ ሴሰኞችንና አመንዝሮችን ግን እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል። (ወደ ዕብራውያን 13፥4)

    በመጀመሪያ ደረጃ እግዚአብሔር ጋብቻን በሁሉ ዘንድ ክቡር ይሁን ነው ያለው በሁሉ ዘንድ ሲል በሴቷም በወንዱም በእስልምናውም በክርስትናውም በማንኛውም የሰው ዘር ሊከበር ይገባዋል ነው የሚለው እንዲሁ እንደቀልድ የሚታይ ነገር አይደለም እንደቀልድ ዛሬ ተገብቶበት ነገ የሚወጣበት እንደዘበት የሚታይ ጉዳይ አይደለም ነው የሚለን ።

  ሌላው ደግሞ ጋብቻ በአንድ ወንድና በአንዲት ሴት መካከል (ይህ ሃሳብ ሊተኮርበት የሚገባው ነው) የሚፈጸም የመንፈስ የነፍስ እና የስጋ ጥምረት ያለበት ነው ይህም ጋብቻ በሁለት ተቃራኒ ጾታ መሃከል የሚፈጸም እና ዘለቄታ ያለው በእግዚአብሔር በቅዱሳን መላአክቱና እና  በሰው ፊት የሚደረግ የቃልኪዳን ትስስር ያለበት ስርዓት ነው ።   

  ዛሬ ዛሬ እንደምናየው ግን የጋብቻን ክቡርነት በዘነጉና ጋብቻ እንዴት እንደተጀመረ ባልተረዱ ግለሰቦችና የጋብቻ አስፈጻሚ ድርጅቶች እንዲሁም የሃይማኖት ድርጅቶች ውስጥ የሚፈጸመው ቅጥ ያጣ እና ስርዓት የሌለው ወንድና ወንድን እንዲሁም ሴትና ሴትን እያጣመሩ ጋብቻን የመሰረቱ የሚመስላቸው ግለሰቦችም ሆኑ ድርጅቶች በምድር ላይ ጥፋትን እንጂ መልካም የሆነን ስርዓት እየፈጽሙ ላለመሆናቸው ሊረዱት ይገባቸዋል። እነዚህን ግለሰቦች ደግሞ እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል ምክንያቱም የእግዚአብሔር ቃል እንዲህ ይላልና   ( … ወይስ ዓመፀኞች የእግዚአብሔርን መንግሥት እንዳይወርሱ አታውቁምን? አትሳቱ፤ ሴሰኞች ቢሆን ወይም ጣዖትን የሚያመልኩ ወይም አመንዝሮች ወይም ቀላጮች ወይም ከወንድ ጋር ዝሙት የሚሠሩ ወይም ሌቦች ወይም ገንዘብን የሚመኙ ወይም ሰካሮች ወይም ተሳዳቢዎች ወይም ነጣቂዎች የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም። 1 ቆሮ 6 : 9-10)

ሴሰኞችንና አመንዝሮችን እግዚአብሔር ከፈረደባቸው ስርዓቱን እያስፈጸሙ ያሉትም ከዚህ ፍርድ የሚያመልጡበት መንገድ አይታየንም ስለዚህ ይህንን ስርዓት ከማስፈጸም ሊታቀቡ ይገባቸዋል አንላለን።

   ከዚህ የባሰው የጥፋቶች ሁሉ ጥፋት ደግሞ ይህንን ስርዓት መንግስት ስለፈቀደውና በሕግ ስለተደገፈ ብቻ እግዚአብሔር የፈቀደው ያህል በእግዚአብሔር እናምናለን የሚሉና እግዚአብሔርን እናገለግላለን የሚሉ ግለሰቦችና የሃይማኖት ድርጅቶች የተቃውሞ ድምጻቸውን ያለማሰማታችውና ዝም የማለታቸው ጉዳይ ስርዓቱን ተስማምተው መቀበላቸውን የሚያሳይ እንጂ ሌላ ምንም ሊሆን እንደማይችል እንገነዘባለን። ትንሽ ቆይቶም እነዚሁ ግለሰቦች ስርዓቱን ለመፈጸም ወይም ጋብቻን ለመፈጸም ወደቤተክርስቲያን ቢመጡ የሚሰጣቸው ምላሽ ምን ሊሆን እንደሚችል መዘንጋት የለብንም ምክንያቱም አስቀድመን የተቃውሞ ድምጻችንን አላሰማንምና ።

   ይህንን ስርዓት እያስፈጸሙ ያሉና ለማስፈጸም ችግር እንደሌለበትና የማያስጠይቃቸው የመሰላቸው ቤተአምልኮዎች ከእግዚአብሔር ሳይሆን ከአባታቸው ከዲያብሎስ ዘነድ የተላኩ የጥፋት መልእክተኞች መሆናቸውን መዘንጋት የለብንም ።

     ስለዚህ በማስጠንቀቅም ይህንን ልላችሁ እወዳለሁ ራሳችሁን ብትመረምሩና ከየት እንደወደቃችሁ ብታስቡና ንስሐ ብትገቡ የትሻለ ነው እላለሁ። በትያጥሮንም ወዳለው ወደ ቤተ ክርስቲያን መልአክ እንዲህ ብለህ ጻፍ፦ እንደ እሳት ነበልባል የሆኑ ዓይኖች ያሉት በእቶንም የነጠረ የጋለ ናስ የሚመስሉ እግሮች ያሉት የእግዚአብሔር ልጅ እንዲህ ይላል፦ ሥራህንና ፍቅርህን እምነትህንም አገልግሎትህንም ትዕግሥትህንም ከፊተኛውም ሥራህ ይልቅ የኋለኛው እንዲበዛ አውቃለሁ። ዳሩ ግን፦ ነቢይ ነኝ የምትለውን ባሪያዎቼንም እንዲሴስኑና ለጣዖት የታረደውን እንዲበሉ የምታስተምረውንና የምታስተውን ያችን ሴት ኤልዛቤልን ስለምትተዋት የምነቅፍብህ ነገር አለኝ፤ ንስሐም እንድትገባ ጊዜ ሰጠኋት ከዝሙትዋም ንስሐ እንድትገባ አልወደደችም። እነሆ፥ በአልጋ ላይ እጥላታለሁ፥ ከእርስዋም ጋር የሚያመነዝሩትን ከሥራዋ ንስሐ ባይገቡ በታላቅ መከራ እጥላቸዋለሁ ልጆችዋንም በሞት እገድላቸዋለሁ፤ አብያተ ክርስቲያናትም ሁሉ ኵላሊትንና ልብን የምመረምር እኔ እንደ ሆንሁ ያውቃሉ፥ ለእያንዳንዳችሁም እንደ ሥራችሁ እሰጣችኋለሁ። (ራእይ 2:18 – 23)

ካሱ ቦስተን 

መንፈሳዊ ትረካ

የመጨረሻው ትንቅንቅ መንፈሳዊ ትረካ ቁጥር 1 ቅዳሜ 02/12/22 ከማለዳው 7:30 ላይ ተለቋል ያዳምጡት ይጠቀሙበታል ይህ ትረካ 38 ክፍሎች አሉት ከቅዳሜ 2/12/22 ጀምሮ በየሳምንቱ ይቀርባል፡ የዩቲዩብ መስመራችንን “kassuboston” ብለው google ላይ ቢፈልጉት በቀላሉ ያገኙታል፤ ሰብስክራይብ የሚለውን ቢጫኑት ትረካውን በየሳምንቱ ማግኘት ይችላሉ። እናመሰግናለን።

ካሱ ቦስተን

እውነተኛ ደቀ መዝሙር

 ክፍል 6

ኢየሱስ ለደቀ መዝሙርነት ብቁ አይደላችሁም ብሎ የርሱን የደቀ መዝሙርነት መለኪያ ያለፉትናና ወደኋላ የተመለሱትን ጥቂት ሰዎች ባለፉት 5 ክፍል ንባባችን ተመልክተናል በዛሬው ክፍል ንባባችን ደግሞ የመጨረሻውን ተሰናባች ሰው እንመልከት ፦

መሰናበት

“ደግሞ ሌላው። ጌታ ሆይ፥ እከተልሃለሁ፤ ነገር ግን አስቀድሜ ከቤቴ ሰዎች እንድሰናበት ፍቀድልኝ አለ።” 

   በዚህ ምእራፍ ውስጥ ይህ የመጨረሻው ጠያቂ ነው። የዚህኛው ደግሞ ብዙም ጊዜ የማይወስድና ቤተሰቡን ብቻ ተሰናብቶ ለመምጣት ስለሆነ የሚፈቀድለት ይመስላል። ግን ምን ተባለ? “ኢየሱስ ግን፦ ማንም ዕርፍ በእጁ ይዞ ወደ ኋላ የሚመለከት ለእግዚአብሔር መንግሥት የተገባ አይደለም አለው።” አሁንም ኢየሱስ ያየው የሰውየውን ልብ ነው። ኢየሱስን ፊት ለፊት እያየው፣ በሥጋ የተገለጠውን ጌታ እየተመለከተ ልቡ ሙሉ በሙሉ ሳይቀልጥ መቅረቱና፣ ቤተሰቦቹን የሚያስብበት ክፍተት ማግኘቱ ፈጽሞ አለመማረኩን ያሳያል። ከኢየሱስ ደቀመዛሙርት ውስጥ ማንም ቤተሰቦቹን የተሰናበተ የለም ሁሉም ተሰናብተው ሳይሆን «ትተው» ነው የተከተሉት። ለመሆኑ መተውና መሰናበት ልዩነት አለው እንዴ? አዎ መተው በክርስቶስ ፍቅር ተሸንፎ በዚያው መቅረት ሲሆን መሰናበት ግን በውሳኔ ላይ ቤተሰብ እንዲሳተፍ መፍቀድ ነው። ሊሰናበት ሲሄድ አሳቡን ሊያስቀይሩት መሞከራቸው አይቀርምና። 

    ጌታን ክርስቶስን ለመከተል ቤተሰብን ይቅርና ሥጋና ደምን (የራስን ማንነት) ማማከር እንኳ አልተፈቀደም። ሐዋርያው ጳውሎስ እግዚአብሔር ልጁን በርሱ ሁኔታ ሊገልጥ በወደደ ጊዜ ከሥጋና ደም ጋር (ከፍጥረታዊ አእምሮውና አስተሳሰቡ) ጋር አልተማከረም። ከርሱ በፊት ሐዋርያት ወደ ነበሩትም አልሄደም። ከሥጋና ከደም ጋርስ አይማከር ከርሱ በፊት ሐዋርያት ወደ ነበሩትስ ለምን አልሄደም? የደቀመዝሙርነት ውሳኔ በማንም ምክርና አስተያየት ተደግፈን የምንወስነው ሳይሆን የራሱ የጠሪው የእግዚአብሔር ዓላማ ገብቶንና የክርስቶስ ፍቅር ነድፎን የምንወስነው ነው። የክርስቶስ ፍቅር ልባችንን ሲነድፈንና የጥሪው ጉልበት ሲነካን ለሌሎች ነገሮች አቅም ያሳጣናል። ደቀመዝሙርነት ኢይሱስን ከመከተል በቀር ሌላ ምንም ነገር ለማድረግ አቅም ማጣት ማለት ነው። የጥሪው ክቡርነትና አጓጊነት ፈጣን ውሳኔን የሚጠይቅ አድርጎታል። 

    ስለዚህ ለዚህ ሰው ኢየሱስ የመለሰው እንዲህ በማለት ነበር፦ “ኢየሱስ ግን፦ ማንም ዕርፍ በእጁ ይዞ ወደ ኋላ የሚመለከት ለእግዚአብሔር መንግሥት የተገባ አይደለም አለው።” (ሉቃ.9:62) እርፍ ማለት ገበሬዎች የሚያርሱበት የእርሻ መሳሪያ ሲሆን ሁለት በሬ ተጠምዶ የሚጎትተውና አራሹ ከኋላ ሆኖ እርፉን በመያዝ ማረሻው መስመሩን ጠብቆ እንዲያርስ የሚጠቀምበት ነው። ጌታ በሚገባው የግብርና ምሳሌ ነው ለዚህ ሰው እየተናገረ ያለው። የተጠመዱት በሬዎች በሙሉ ኃይላቸው ወደፊት እየጎተቱ ባሉበት ሰዓት እርፉን የጨበጠው ገበሬ ወደኋላ ሊመለስ ቢል አይችልም።የበሬዎቹ ጉልበት ወደፊት ይጎትተዋል። ሊመለስ ከወሰነ ግን አንድ ነገር ማድረግ አለበት ይህም እርፉን መልቀቅ ነው። 

   በዚህ ምሳሌ መሰረት የእግዚአብሔር መንግስት ወደፊት የምትዘረጋና ወደ ፍጻሜ እየችኮለች ያለች መንግስት ናት። ወደ ኋላ የሚመለከቱትን ቆማ ልትጠብቃቸው አትችልም። እግዚአብሔር ዘለዓለማዊ የሆነውን የመንግስቱን ሐሳብ ለመፈጸም እየተራመደ ነው። የእግዚአብሔር ዘለዓለማዊ አሳብ ሁሉም በጊዜው እንዲፈጸም ስለተወሰነ እኛ አንድ ነገር አድርገን እስክንመጣ ድረስ ሊጠብቀን የሚችል አይደለም። የእግዚአብሔር መንግስት ተንቀሳቃሽ መንግስት ናት።በርስዋ ውስጥ ከገባን በኋላ በርስዋ የእንቅስቃሴ ስልት ብቻ ነው ልንንቀሳቀስ የምንችለው። በእግዚአብሔር መንግስት ወስጥ ከገባን በኋላ የራሳችን እንቅስቃሴ ሊኖረን አይችልም። ህይወታችን ሁሉ በርስዋ የእንቅስቃሴ ምህዋር ውስጥ ይመራል። 

    የእግዚአብሔርን መንግስት የያዝንባትና መንግስቱ እኛን የያዘችበት ዕለት የኛ እንቅስቃሴና ዓላማ ሁሉ ያበቃበት፣ የሞተበት፣ የተቀበረበት ቀን ነው፡፤ እናትና አባትን ለመቅበር የምንፈልግበት ቀን ሳይሆን ራሳችንን ለዚህ ዓለም የምንቀብርበትና በመንግስቱ ውስጥ ትንሳኤን የምናገኝበት ድንቅ ዕለት ነው። መቸም ራሱ የሞተና የተቀበረ ሰው እናት አባቱን ሊሰናበትም ሊቀብርም አይጠይቅም ተቀብሮአልና። 

     ገበሬው እርፉን ለሚጎትተው የበሬዎች ኃይል መገዛትና እርፉን ጨብጦ እነርሱ ወደሚሄዱበት አቅጣጫ ብቻ መሄድ እንደሚገባው ሁሉ አንድ ደቀ መዝሙርም የእግዚአብሔርን መንግስት ማለትም ክርስቶስን ካገኘ በኋላ ለመንግስቱ ጉልበት ተሸንፎ መንግስቱ ወደምትሄድበት አቅጣጫ ብቻ የሚሄድ ነው። “ነፋስ ወደሚወደው ይነፍሳል፥ ድምፁንም ትሰማለህ፥ ነገር ግን ከወዴት እንደ መጣ ወዴትም እንዲሄድ አታውቅም፤ ከመንፈስ የተወለደ ሁሉ እንዲሁ ነው።” (ዮሐ.3፡8) ከእግዚአብሔር የተወለደ የመንግስቱ ደቀመዝሙር በነፋስ መመሰሉና ከወዴት እንደመጣ ወዴትም እንደሚሄድ አለመታወቁ ለምን ይሆን? በራሱ መንገድና መርህ «እናቴንና አባቴን ልቅበር ልሰናበት» በሚለው መርህ መመላለስ አቁሞ በመንግስተ ሰማያት ምህዋር ውስጥ ስለገባ አይደለምን? እናቱንና አባቱን ሊቀብርና ሊሰናበት የሚሄደውንማ ሁሉም ሰው ከየት እንደመጣ ወዴትም እንደሚሄድ ያውቀዋል የሰው ሁሉ ምልልስ ነውና። ከእግዚአብሔር ተወልደን የክርስቶስን ማንነት ተካፍለን «ከመንፈስ የተወለደ» ስንሆን ግን እንቅስቃሴአችን ሁሉ በእግዛኢብሔር ዙፋን የሚመራ፣ በጉ ወደሚሄድበት ብቻ የሆነ ለሰዎች የማይታይና በሰዎች የማይገመት ይሆናል። ዓለም የሰው ልጆች እንዲመላለሱበት በቀረጸችው የኑሮ መርህ ሳይሆን በእግዚአብሔር መንግስት ስርዓት እንመላለሳለን። የሂደታችን አቅጣጫ ሰዎች ወደሚሄዱበት አይደለም በጉ ወደሚሄድበት እንጂ። እንደ ነፋስ በዚህ ዓለም እንዳለን ይታወቃል፣ ሰዎች ድምጻችንን ይሰማሉ፣ የእንቅስቃሴአችንን ዱካ ግን ሊያውቁ አይችሉም። እንቅስቃሴአችን በጣም ዝቅተኛ ከሆነው የሰው ልጆች መርህ ወጥቶ በመንግስቱ መንኮራኩር ውስጥ ተሰውሮአልና። 

    የእንቅስቃሴአችን እዝ ማእከል እግዚአብሔር እንጂ ስጋና ደም፣ የምድር ሥርዓት፣ ፖለቲካ፣ ምድራዊ ጥበብ በጭራሽ አይደለም። ወደ መንግስቱ ስንመጣ የመንግስቱ ጉልበት ዑደት (አዙሪት) ወደርሱ ጎትቶ ካላስገባንና ለዚህ ሰማያዊ ጉልበት ወዲያው ተሸንፈን ኢየሱስን ካልተከተልን የመንግስተ ሰማይ ደቀመዝሙር አይደለንም።  ይቀጥላል 

ካሱ ቦስተን

እባክዎን ካነበቡ በኋላ ላይክ የሚለውን ይጫኑ እንዲሁም መልእክቱን ለሌሎች ያካፍሉ አመሰግናለሁ ።

እውነተኛ ደቀ መዝሙር

ክፍል 5

በዛሬው ክፍል ንባባችን ደግሞ የጌታ ደቀመዝሙርነትን መስፈርት ማሟላት አቅቶት እናትና አባቱን ለመቅበር ስለተመለሰ አንድ ሰው እንመልከት ፦

አባቴንና እናቴን ልቅበር

“ሌላውንም። ተከተለኝ አለው። እርሱ ግን፦ ጌታ ሆይ፥ አስቀድሜ ልሂድና አባቴን እቀብር ዘንድ ፍቀድልኝ አለ።” (ሉቃ.9፡59)

የዚህን ሰው ምክኒያት ስንመለከት ይህስ በጣም አሳማኝ ምክንያት ነው ብለን እንል ይሆናል። ለዚህስ ፈቃድ የሚከለክል ማን ሊኖር ይችላል? በጣም ክፉ የተባለ አለቃ ቢኖረን እንኳ ለዚህስ ልቡ ይራራል። እንዲያውም ከቻለ ራሱም ቀብሩ ላይ ሊመጣ ይሞክራል እንጂ፡ ኢየሱስስ? ኢየሱስማ ለደቀመዝሙር የተቀመጠውን መለኮታዊ መለኪያ ለቀብር ብሎ አይሽርም። ምንም ነገር ከደቀመዝሙርነት በልጦ ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባ ነገር ሊኖር አይችልም። 

   ኢየሱስን ከመከተላችን በፊት ልናደርገው የሚገባ ምንም ነገር የለም። ስለዚህ መምህሩ እንዲህ መለሰለት “ኢየሱስም፦ ሙታናቸውን እንዲቀብሩ ሙታንን ተዋቸው፤ አንተስ ሄደህ የእግዚአብሔርን መንግሥት ስበክ አለው።” በእውነተኛው ወንጌል የእግዚአብሔር መንግስት ከሁሉ ትበልጣለች። ለሙታን ህይወት የሚሰጠውን የእግዚአብሔርን መንግስት ምንም ነገር ከማይሰጡ ነገሮች ጋር ልናወዳድረው አይገባንም። በዚህ ስፍራ ኢየሱስ ስለ አንድ ጊዜ ክስተት ብቻ ሳይሆን አንድ ደቀመዝሙር በዘመኑ ሁሉ መከተል ያለበትን መርህ ነው ያስቀመጠው። 

    ምናልባት እንደሰው አስተሳሰብ ይህ ሰው ዘመኑን ሁሉ ጌታን ሊከተል ከሆነ አንድ ጊዜ ሄዶ እናቱንና አባቱን ቀብሮ ጣጣውን ጨርሶ ቢመጣ ምን አለበት? እንል ይሆናል። ነገር ግን ይህ ጥያቄ የአንድ ጊዜ ክስተትን ብቻ የሚያመለክት ሳይሆን ሰውየው ለነገሮች የሚሰጠውን ቅደም ተከተልና በህይወቱ ሁሉ የሚጠቀምበትን የህይወት ሚዛን የሚያሳይ ነው። ዛሬ እናት አባቱን መቅበር ኢየሱስን ከመከተል የሚቀድም ሆኖ ከታየው ነገም ሌላ ችግር ሲገጥመው አንገብጋቢውንና ዋናውን የእግዚአብሔር አጀንዳ ትቶ ይሄዳል። በህይወቱ ሁልጊዜ ከመንግስቱ ሥራ ይልቅ በሰዎች ዘንድ የተለመደው የኑሮ ሥርዓት እና ማህበራዊ ህይወት ይቀድምበታል። እነዚህ የማህበራዊ ኑሮ ክስተቶች ደግሞ እስከ ህይወቱ ፍጻሜ ድረስ የሚያቋርጡ አይደሉም። አንድ ሲሄድ አንዱ ይመጣል። ዛሬ አባቴንና እናቴን ልቅበር ያለው ሰው ነገ አጎቴንና አክስቴን ከነገ ወዲያ ደግሞ ሚስቴንና ልጄን እያለ እስከ ህይወቱ ፍጻሜ ድረስ በምክንያት ገመድ ወደ ኋላ እየተጎተተ ይኖራል። ስለዚህ ኢየሱስ እዚህ ጋ እያፈረሰ ያለው የሰውየውን አስተሳሰብ ነው። ኢየሱስ በመልሱ ውስጥ አንድ ሁላችንም በቅጡ ልንረዳው የሚገባንን ሚስጢር ገልጦአል። ይህም ማን ምን መስራት እንዳለበት ማወቅ እንዳለብን ነው። ይህ ሰው እርሱ ሊሰራው የማይገባውን ነገር ነበር ለመስራት የጠየቀው። በዚህም የኢየሱስ ደቀ መዝሙር ሊሰራው የማይገባውንና የሚገባውን ነገር አስቀድመን ማወቅ እንዳለብን እንረዳለን። 

    ለምን ደቀ መዝሙር እንደሆንንና ደቀ መዝሙር ሊሰራ የሚገባውን፣ ካላወቅን ደቀመዝሙር መሆን አንችልም። ደቀመዝሙር ያሰኘን አንዱን ጌታ ብቻ መከተላችንንና እርሱ የመጣበትን ዓላማ ለማስፈጸም መጠራታችን ነው። የደቀመዝሙር ሥራ ጌታው ክርስቶስ ህይወቱን የሰጠበትን የመንግስቱን ወንጌል መስበክንና ሰዎችን ወደ ህይወት ማምጣት ሲሆን የሙታን ሥራ ደግሞ ሙታናቸውን መቅበር ነው። እንግዲህ ይህ ሰው ሙታንን ለመቅበር በመጠየቁ ከማን ወገን መሆኑን አረጋግጦአልና የኢየሱስ ደቀመዝሙር ሊሆን አይችልም። ሙታን የተባሉት ማለትም በበደላቸውና በኃጢአታቸው ሙታን የሆኑት ሙሉ ጊዜአቸውንና ኃይላቸውን ጥበባቸውን የሚያውሉት የእግዚአብሔር መንግስት አጀንዳ ያልሆነ የራሳቸውን ሙት ስርዓት ለማስፈጸም ነው። ዓለም ይህንን የሙታን ስርዓት ለማስፈጸም በሚችል በጣም ብዙ ህዝብ ተሞልታለች። አብዛኛው የዓለም ህዝብ ሙት እስከሆነ ድረስ የፖለቲካውን አመራር የሚመሩ፣ አገር የሚያስተዳድሩ፣ የሚነግዱ ብዙዎች ናቸው። እቁቡ፣ እድሩ፣ ቀብሩ፣ ፓለቲካው ፣ንግዱ፣ በእልፍ አእላፍ ሙታን የተሞላ ነው። ሁሉም ሲታይ ሰዎች እጅብ ብለውበታል። የሞተ ሰው ስለመቅበርም ቢሆን ከዘመን ለውጥና ከብዙ የሥራ ውጥረት የተነሳ እንደ ድሮው ለነፍሴ ብሎ የሚቀብር እየመነመ ቢመጣም ራሱን የሚቀብረው እንዳያጣ የሚፈራ ሁሉ በተለያየ ስም በመደራጀት ሲያከናውን ይታያል። ይህ እንግዲህ በሙታን በተሞላችው ዓለም የሚታየው ሁኔታ ነው። 

      በሌላው ጎራ ደግሞ ከጨለማ ወደሚደነቅ ብርሃን የተጠሩ ጥቂት የጌታ ደቀመዛሙርት የአለም ብርሃን ለመሆንና ለዚህች በሙታን ለተሞላች አለም የክርስቶስን ህይወት ለማድረስ የተሰበሰቡ አሉ። በአለም ካለው ህዝብ ጋር እነዚህን ስናያቸው በጣም ጥቂቶች ናቸው። የያዙት ዓላማ ግን ሙታኑ ከያዙት ጋር የማይነጻጸር ፈጽሞ የተለየ ለሰው ልጆች ሁሉ መዳንን የሚሰጥ የመንግስቱን ወንጌል ነው። በሙታኑ ጎራ ብዙ ትጉ ሰራተኞች ቢኖሩም በህያዋኑ ጎራ ያሉት ግን ጥቂቶች በመሆናቸው “የመከሩ ጌታ ሰራተኞችን እንዲልክ ጸልዩ ተብለናል። 

ነገሩ እንዲህ ግልጽ ከሆነልን በክቡር ጥሪ ተጠርቶ ወደ ጥቂቶች ጎራ የገባ የኢየሱስ ደቀመዝሙር ብዙሃኑን ሙታን ለመርዳት ወደእነርሱ ይሻገር ዘንድ አይሆንለትም። እነርሱ በጣም ብዙዎች ናቸው። ዓላማቸውም ያንን የሞተ ሥራ ብቻ መፈጸም ብቻ ነው እንጂ የእግዚአብሔር መንግስት አይደለም። ስለዚህ ሙታናቸውን ይቀብሩ ዘንድ ሙታንን ትተን የመንግስቱን ወንጌል እንሰብክ ዘንድ ይገባናል።  ይቀጥላል፤ 

ካሱ ቦስተን

እባክዎን ካነበቡ በኋላ ላይክ የሚለውን ይጫኑ እንዲሁም መልእክቱን ለሌሎች ያካፍሉ አመሰግናለሁ ።

እውነተኛ ደቀ መዝሙር

ክፍል 4

ባለፈው ክፍል 3 ጽሁፍ እንዳየነው ባለጸጋው ሰው የጌታ ደቀመዝሙርነትን መስፈርት ማሟላት አቅቶት ሲመለስ አይተን ለዛሬ ሌላ ሰው ለማየት ተቀጣጥረን ነበር ይህንን ሰው ደግሞ እንመለከታለን አብረን እናንብበው።

አንድ ሰው

“እነርሱም በመንገድ ሲሄዱ አንድ ሰው። ጌታ ሆይ፥ ወደ ምትሄድበት ሁሉ እከተልሃለሁ አለው። ኢየሱስም፦ ለቀበሮዎች ጕድጓድ ለሰማይም ወፎች መሳፈሪያ አላቸው፥ ለሰው ልጅ ግን ራሱን የሚያስጠጋበት የለውም አለው።(ማቲ 8፤19-20)” 

   ኢየሱስ ለሰዎች የሚመልሰው በአፋቸው የተናገሩትን በመስማት ብቻ ሳይሆን በልባቸው የነበረውንም አሳብ ያውቅ ስለነበር ከዚያ በመነሳት ትክክለኛና አፋቸውን ሳይሆን ልባቸውን የሚመጥን መልስ ነው የሚነግራቸው። ሰለዚህ ብዙ ጊዜ የጠያቂዎችን የውስጥ ፍላጎትና ምኞት እንዲሁም ትክክለኛ ማንነታቸውን የምናገኘው በሰዎቹ ጥያቄ ሳይሆን በኢየሱስ መልስ ውስጥ ነው። 

    ይህ ሰው ኢየሱስ ወደሚሄድበት ሁሉ መከተል ነው የፈለገው። ነገር ግን ኢየሱስ እያደረገ የነበረውን ተአምራትና የሚከተለውን ብዙ ህዝብ ስላየ በልቡ ከኢየሱስ ጋር ከሄደ ምንም እንደማይቸገር አስቦአል። ይህን አሳቡን ያወቀው ጌታ እርሱን ከመከተሉ በፊት ራሱን እንዲክድ መጠየቁ ነው። ምክንያቱም መኖሪያና መተዳደሪያን ተስፋ አድርጎ ወይም ከኢየሱስ ጋር ከሆንኩ አልቸገርም ብሎ ኢየሱስን መከተል ራስን አለመካድ ነውና። ስለዚህ ኢየሱስ ለዚህ ሰው ምንም ነገር ከእርሱ ጠብቆ (ማለትም አንድ ነገር አገኛለሁ ብሎ እንዳይከተለው) የርሱ ኑሮ ከሰማይ ወፎችና ከምድር ቀበሮዎች ያነሰ እንደሆነ አሳየው። ራሱን ካልካደ በቀር ከሰማይ ወፎችና ከምድር ቀበሮዎች ያነሰን ኑሮ የሚኖር ሰው እንዴት ሊከተል ይችላል? 

ለመሆኑ እኛ እንደዚህ አይነቱን የመጽሐፍ ቅዱስ ኢየሱስ ነው እየተከተልን ያለነው? ወይስ ሰዎች በምኞታችንና በፍላጎታችን ልክ በአእምሮአችን የሳሉብንን በመፅሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሌለ ኢየሱስ? 

    ብዙዎች የሚከተሉትን ኢየሱስ ሲናገሩ ስሰማ ምንም መከራ እንዳያገኛቸው የሚንከባከባቸውን፣ ከጎረቤቶቻቸው ሁሉ ይልቅ ያበለጸጋቸውን፣ የተመኙትን ሁሉ አንድም ሳያስቀር የፈጸመላቸውን ኢየሱስ ነው። ይህ ደግሞ የመጽሐፍ ቅዱሱ ኢየሱስ አይደለም። ጌታ ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ ሲናገር እንዲህ ነው ያለው “በዓለም ሳላችሁ መከራ አለባችሁ፤ ነገር ግን አይዞአችሁ፤ እኔ ዓለምን አሸንፌዋለሁ።” (ዮሐ.16:33) በዚህ መንገድ እየተራመደ የነበረው ሐዋርያም “ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ፥ ወይስ ጭንቀት፥ ወይስ ስደት፥ ወይስ ራብ፥ ወይስ ራቁትነት፥ ወይስ ፍርሃት፥ ወይስ ሰይፍ ነውን? ስለ አንተ ቀኑን ሁሉ እንገደላለን፥ እንደሚታረዱ በጎች ተቆጠርን ተብሎ እንደ ተጻፈ ነው። በዚህ ሁሉ ግን በወደደን በእርሱ ከአሸናፊዎች እንበልጣለን።” በማለት ያውጃል። (ሮሜ.8፡35) በሌላም ስፍራ “ይህ ስለ ክርስቶስ ተሰጥቶአችኋልና፤ ስለ እርሱ መከራ ደግሞ ልትቀበሉ እንጂ በእርሱ ልታምኑ ብቻ አይደለም፤” በማለት ቅዱሳንን ያጽናናል። (ፊል.1፡29) 

    እኛ የክርስቶስ ተከታዮች ከሆንን ክርስቶስ በሥጋ በዓለም ሳለ ከኖረው ኑሮና ከተመላለሰበት ምልልስ የተለየ ልንንኖር አንችልም። እርሱን ያሰቃየችና ያሳደደች ዓለም እኛን በመልካም ተቀብላ ባለጸጎችና ሁሉ የተመቻቸው ካደረገችን ግን የኢየሱስ ተከታዮች አይደለንም። ይህንንም ጌታችን አስረግጦ ሲናገር “ዓለም ቢጠላችሁ ከእናንተ በፊት እኔን እንደ ጠላኝ እወቁ። ከዓለምስ ብትሆኑ ዓለም የራሱ የሆነውን ይወድ ነበር፤ ነገር ግን እኔ ከዓለም መረጥኋችሁ እንጂ ከዓለም ስለ አይደላችሁ ስለዚህ ዓለም ይጠላችኋል። ባርያ ከጌታው አይበልጥም ብዬ የነገርኋችሁን ቃል አስቡ። እኔን አሳደውኝ እንደ ሆኑ እናንተን ደግሞ ያሳድዱአችኋል፤ ቃሌን ጠብቀው እንደ ሆኑ ቃላችሁን ደግሞ ይጠብቃሉ።” ብሎአል (ዮሐ.15፡18) አዎ ባሪያ ከጌታው አይበልጥም። 

    በዚህ ቃል መለኪያ ዛሬ በምድር ላይ ክርስቶስ ያልኖረውን ምቹ ኑሮ የሚኖሩና በወንጌል ስም በከፈቱት ንግድ በልጽገው ያሉ ሁሉ ከጌታቸው መብለጣቸው ነው ወይስ ባሪያ አይደሉም? ባሪያስ ከጌታው አይበልጥም ባሪያ ባይሆኑ ነው እንጂ። ይህን ስንል መከራን ወይንም ማጣትን ጠርተን እናመጣዋለን እያልን ሳይሆን በምንሸከመው መስቀልና በተከተልነው መምህር ውስጥ የተካተቱ ስጦታዎች ናቸው። ማንም ክርስቶስን ሰብኮ የማይሰደድ በብዙ መከራና ስቃይ የማያልፍ የለም። ” በእውነትም በክርስቶስ ኢየሱስ እግዚአብሔርን እየመሰሉ ሊኖሩ የሚወዱ ሁሉ ይሰደዳሉ።” (2.ጢሞ.3፡12) ተብሎ ተጽፎአልና። ሁሉም እጁን ዘርግቶ ከተቀበለንና ካልተሰደድን ግን መልሱ ግልጽ ነው በክርስቶስ ኢየሱስ እግዚአብሔርን እየመሰል አልተመላለስንም። መመላለስ በጀመርንበት ቅጽበት ግን ስደቱ መከራው ያን ጊዜውኑ ይጀምራል። እንግዲህ ይህንን ከላይ ያየነውን ሰው የጠራው ኢየሱስ ምንም የሌለው ኢየሱስ ነው። ራሱን ኢየሱስን ወዶ ካልሆነ 

«ኢየሱስ አንድ ነገር ይሰጠኛል» ብሎ ሊከተለው እንዳይሞክር ምንም እንደሌለው ገልጾ አሳየው። ያመንከው ኢየሱስ ይህንን ነው? ከሆነ መልካም።  

    እንግዲህ ኢየሱስን መከተል ወይም ደቀመዝሙር መሆን ሌላ ምንም ሳይፈልጉ ኢየሱስ እንደኖረና እንደተመላለሰ መኖር ብቻ ነው። ይቀጥላል።

ካሱ ቦስተን

እባክዎን ካነበቡ በኋላ ላይክ የሚለውን ይጫኑ እንዲሁም መልእክቱን ለሌሎች ያካፍሉ አመሰግናለሁ ።