• “ትቀደሱም ዘንድ ፈልጉ”

    መጽሃፍ ቅዱስ በዕብራውያን 12:14 ላይ (ህያው ቃል ከተሰኘው መጽሃፍ ቅዱስ የተወሰደ) “ከማንም ሰው ጋር ተስማምታችሁ በሰላም ኑሩ ቅድስና የተሞላበትንም ህይወት ለመኖር ፈልጉ ምክኒያቱም ያለቅድስና ህይወት ጌታን ማየት ፈጽሞ አይቻልምና ” በማለት ያሰፈረው ቃል ላይ ቅድስና የተሞላበት ህይወት ለመኖር ፈልጉ ሲለን ይህ ሃሳብ ጌታ ኢየሱስን እንደግል አዳኛችን አድርገን ከተቀበልንበት ጊዜ ጀምሮ ያለውና ወደፊትም የምንኖረው ህይወት በቅድስና ህይወት ይሁን ነው እያለን ያለው።

        ቅድስና ከደህንነታችን ቀጥሎ ትልቅ ግምት ልንሰጠው የሚገባ የህይወት ክፍላችን ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ የበደላችንንና የሃጢዓታችንን ዋጋ ከከፈለ በኋላ በዕምነት ወደ እርሱ ቀርበን የጽድቁ ተካፋይ እንሆን ዘንድ ተጋብዘናል ግብዣውንም ተቀብለን በጸጋው የጽድቁ ተካፋዮች ሆነናል። ይህ ማለት ግን በምድር የሚኖረንን የቅድስናና የጽድቅ ህይወት ፈጽመን አበቃን እንደፈለግን እንኑር ማለት ግን አይደለም ይልቁንም ጀመርነው እንጂ።  

        ቅድስና በአንድ ቀን አዳር ወይም በአንድ ቀን ጸሎት የምንከውነው ሳይሆን የእድሜ ልክ ልምምድና ኑሮ መሆኑን ልንገነዘበው ይገባናል። ለዚህ ነው የእግዚአብሄር ቃል “ትቀደሱም ዘንድ ፈልጉ” የሚለን በአጭር መንገድ ተጉዘን ቅድስናን አግኝተን ጨርሰነዋል ማለት ሳይሆን ሳንታክት ሳናቋርጥ ዘወትር በጽናትና በትዕግስት የምንፈልገውና የምንፈጽመው ወደተሰጠንም ወደ እግዚአብሄር ክብር የምንተላለፍበት ብቸኛው መንገድ ነውና ሳንታክት በቅድስናና በንጽህና ለመኖር እንፈልግ ብዬ የዛሬውን መልዕክቴን በዚሁ አጠናቅቃለሁ። ተባረኩ ።

    ካሱ ቦስተን

  • የዘላለም ህይወት እንዳለን እርግጠኛ ነን ?

    ክፍል 6

    የእግዚአብሔር ልጅ መሆን !

    በክፍል 5 ንባባችን ላይ ክርስቶስ ቅጣታችንን እንደተቀበለ ተመልክተናል። ክርስቶስ ስለእኛ ሲል በመስቀል ላይ እስከሞት ድረስ ያደረሰው እግዚአብሄር ለእኛ ያለውን ታላቅ ፍቅር መግለጫ እንደሆነ እናስተውል፤ በሌላ መልኩ ደግሞ ስንመለከተው አንድ የሚያስገኝልን ትልቅ የእግዚአብሄር ልጅነት ስልጣን ነው። በመስቀል ላይ የሞተልንን ጌታ ኢየሱስን አምነን የዘላለም ህይወት ወራሽ ከመሆናችን ጋር የምንወርሰው የልጅነት ስልጣን እንደሆነ በገላቲያ 3፡26-27 እንዲህ ይላል፡- ‹‹በእምነት በኩል ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጆች ናችሁና፤››፡፡ ሁላችን የእግዚአብሔር ልጆች የመሆን ፍላጎት ቢኖረንም ይህ ሊሳካ የሚችለው በእምነት በኩል እንደሆነ ጥቅሱ ያስረዳል፡፡ በክርስቶስ ላይ ያለን እምነት ነው የእግዚአብሔር ልጆች እንድንሆን የሚያደርገን፡፡

    ዮሐንስ 1፡12-13 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ለተቀበሉት ሁሉ ግን፥ በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው፤››፡፡ ይህ ጥቅስ የእግዚአብሔር ልጅነት ስልጣን የተሰጣቸው እነማን እንደሆኑና ከእግዚአብሔር መወለድ ማለት ምን ማለት እንደሆነ ይነግረናል፡፡ የልጅነት ስልጣኑ የተሰጠው ክርስቶስን ለተቀበሉ ሲሆን ይህን የሚያደርጉ አማኞች ከእንግዲህ ወዲያ ፍጥረታዊ ሰዎች ብቻ እንዳልሆኑ ጥቅሱ ያበስራቸዋል፡፡

    የእግዚአብሔር ልጅና ቤተሰብ ለመሆን ዳግም መወለድ ይኖርብናል፡፡ ጌታችን በዮሐንስ 3፡3 ላይ እንዲህ ያለ ማስጠንቀቂያ ያስተላልፍልናል፡- ‹‹ኢየሱስም መልሶ:- እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም አለው››፡፡ በመቀጠል በዮሐንስ 3፡5 ላይ እንዴት ይህ ዳግም ልደት እንደሚከናወን ያስረዳናል፡- ‹‹ኢየሱስም መለሰ፥ እንዲህ ሲል:- እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም››፡፡

    መንግስተ ሰማይን የሚወርሱት የእግዚአብሐር ልጆች ብቻ ናቸው፡፡ በ1ጴጥሮስ 1፡4 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን በመነሣቱ ለሕያው ተስፋና ለማይጠፋ፥ እድፈትም ለሌለበት፥ ለማያልፍም ርስት እንደ ምሕረቱ ብዛት ሁለተኛ የወለደን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክና አባት ይባረክ፤ ይህም ርስት በመጨረሻው ዘመን ይገለጥ ዘንድ ለተዘጋጀ መዳን በእምነት በእግዚአብሔር ኃይል ለተጠበቃችሁ ለእናንተ በሰማይ ቀርቶላችኋል››፡፡ በክርስቶስ በማመን የእግዚአብሔር ልጅ ሆነዋል? ይህን ካላደረጉ በእግዚአብሔር ቃል መሰረት በሰማይ ርስት የሎትም፡፡

    ወድ አንባቢዬ የዘላለም ህይወት እንዳለን እርግጠኛ ነን በሚል ሃሳብ በተከታታይ ከክፍል 1 ጀምሮ እስከዚህኛው ክፍል ድረስ አብራችሁ ስላላችሁ አመሰግናለሁ ቀጣዩን ክፍልም አብረን እንቀጥላለን እስከዚያው ቸር እንሰንብት

    ካሱ ቦስተን

  • የዘላለም ህይወት እንዳለን እርግጠኛ ነን ?

    ክፍል 5

    ክርስቶስ ቅጣታችንን ተቀብሎልናል !

    ሁላችን ኃጢአትን አድርገናል፡፡ እግዚአብሔር ጻድቅ ፈራጅ ስለሆነ ለኃጢአታችን የሚገባንን ፍርድ ልንቀበል ይገባናል፡፡ ይህም ደሞዝ ሞት ነው፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር ፍቅር ስለሆነ ልጁ ኢያሱስ ክርስቶስ ይህንን ቅጣት በእኛ ፈንታ ተቀብሎልናል፡፡ ሮሜ 5፡6-10 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ገና ደካሞች ሳለን ክርስቶስ ዘመኑ ሲደርስ ስለ ኃጢአተኞች ሞቶአልና››፡፡ ይህን ፍቅር ለመረዳት አዳጋች ነው፡፡

    በተጨማሪ 1ጴጥሮስ 3፡18 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ክርስቶስ ደግሞ ወደ እግዚአብሔር እንዲያቀርበን እርሱ ጻድቅ ሆኖ ስለ ዓመፀኞች አንድ ጊዜ በኃጢአት ምክንያት ሞቶአልና፤ በሥጋ ሞተ በመንፈስ ግን ሕያው ሆነ››፡፡ ዳግመኛ ወደ እግዚአብሔር እቅፍ እንድንመለስ ጻድቅ የሆነው ክርስቶስ ኃጥኣን በሆነው በእኛ ፈንታ መሰቃየት ነበረበት፡፡ ‹‹እኛ በእርሱ ሆነን የእግዚአብሔር ጽድቅ እንሆን ዘንድ ኃጢአት ያላወቀውን እርሱን ስለ እኛ ኃጢአት አደረገው›› (2ቆሮንቶስ 5፡21)፡፡ ክርስቶስ እኛ ፈጽሞ ልንሰራው የማንችለውን ሥራ ሰርቶልናል፡፡ እዳችንን ከፍሎልናል፡፡ የሰው ልጅ ይህንን እዳ መክፈል ቢችል ኖሮ ክርስቶስ በመስቀል ላይ መሞት ባላስፈለገው ነበር፡፡ በበደላችን ሙታን ነበርን፣ ነገር ግን ከወደደን ከታላቅ ፍቅሩ የተነሳ ክርስቶስ በእኛ ፈንታ እንዲሞት በማድረግ የጽድቅ ፍርዱ ሳይዛባ ከሞት አዳነን፡፡

    ሰው የሚድንበት ብቸኛ መንገድ ክርስቶስ ብቻ ነው፡፡ ሌላ ምንም አማራጭ የለንም፡፡ ዮሐንስ 14፡6 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ኢየሱስም፡- እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ፤ በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም››፡፡ ወደ እግዚአብሔር የምንደርስበት መንገድ ክርስቶስ ነው፡፡ በተጨማሪ የሐዋሪያት ሥራ 4፡12 እንዲህ ይላል፡- ‹‹መዳንም በሌላ በማንም የለም፤ እንድንበት ዘንድ የሚገባን ለሰዎች የተሰጠ ስም ከሰማይ በታች ሌላ የለምና››፡፡ በሙሐመድ፣ በቡድሃ፣ በአይሁድንት፣ ወይም በሌሎች በማናቸውም የሃይማኖት ስሞች መዳን የለም፡፡ እኛ በፈጠርነው የክርስትና ሃይማኖት ስርአቶችም ጭምር መዳን የለም፡፡ ድነታችን የምናገኘው እዳችንን በከፈለው በክርስቶስ ብቻ ነው፡፡

    እዳችንን ለመክፈል ክርስቶስ ተሰቃይቷል፡፡ የተቀበለውን መከራ ማሰብ አእምሮችን ፈጽሞ አይችልም፡፡ ክርስቶስ ወደዚህ አለም የመጣው በሞቱ እዳችንን ለመክፈል ነው፡፡ የክርስቶስን ሞት የሚተነብዩ በርካታ የብሉይ ኪዳን ጥቅሶች አሉ፡፡ ለአብነት ያህል ክርስቶስ ከመሞቱ ከ700 አመት በፊት የተነገረው የኢሳይያስ ትንቢት አንዱ ነው፡- ‹‹እርሱ ግን ስለ መተላለፋችን ቈሰለ፥ ስለ በደላችንም ደቀቀ፤ የደኅንነታችንም ተግሣጽ በእርሱ ላይ ነበረ፥ በእርሱም ቍስል እኛ ተፈወስን። እኛ ሁላችን እንደ በጎች ተቅበዝብዘን ጠፋን፤ ከእኛ እያንዳንዱ ወደ ገዛ መንገዱ አዘነበለ፤ እግዚአብሔርም የሁላችንን በደል በእርሱ ላይ አኖረ›› (ኢሳይያስ 53፡5-6)፡፡ የክርስቶስ ሞት ድንገተኛ አይደለም፣ የሰውን ልጅ ለመቤዠት የእግዚአብሔር ዘላለማዊ እቅድ እንጂ፡፡

    ክርስቶስ ሁሉን በማወቅ ችሎታው ሊሆንበት ያለውን ሁሉ ያውቅ ነበር፡፡ በማቴዎስ 20፡17-19 እንዲህ የሚል ቃል እናነባለን፡- ‹‹ኢየሱስም ወደ ኢየሩሳሌም ሊወጣ ሳለ፥ በመንገድ አሥራ ሁለቱን ደቀ መዛሙርት ብቻቸውን ወደ እርሱ አቅርቦ። እነሆ፥ ወደ ኢየሩሳሌም እንወጣለን፣ የሰው ልጅም ለካህናት አለቆችና ለጻፎች ይሰጣል፤ የሞት ፍርድም ይፈርዱበታል፥ ሊዘባበቱበትም ሊገርፉትም ሊሰቅሉትም ለአሕዛብ አሳልፈው ይሰጡታል፥ በሦስተኛውም ቀን ይነሣል አላቸው››፡፡ ክርስቶስ ያለማንም አስገዳጅነት በፈቃዱ በእኛ ፈንታ ሊሞትልን ወሰነ፡፡

    ክርስቶስ በተዋህዶ ሰውም አምላክም ነው፡፡ ሊሆንበት ያለውን ከማወቅ ባሻገር ሥጋ እንደመልበሱ በሞቱ ተጨንቆ ነበር፡፡ ኢየሱስ ከሞቱ ቀን ቀደም ብሎ ባለው ምሽት በጌቴ ሰማኒ የአታክልት ሥፍራ በነበረበት ወቅት የነበረውን ሁኔታ በሉቃስ 22፡41-44 እንዲህ እናነባለን፡- ‹‹ከእነርሱም የድንጋይ ውርወራ የሚያህል ራቀ፥ ተንበርክኮም። አባት ሆይ፥ ብትፈቅድ ይህችን ጽዋ ከእኔ ውሰድ፤ ነገር ግን የእኔ ፈቃድ አይሁን የአንተ እንጂ እያለ ይጸልይ ነበር። ከሰማይም መጥቶ የሚያበረታ መልአክ ታየው። በፍርሃትም ሲጣጣር አጽንቶ ይጸልይ ነበር፤ ወዙም በምድር ላይ እንደሚወርድ እንደ ደም ነጠብጣብ ነበረ››፡፡ ክርስቶስ በእርግጥም በመስቀሉ ምጥ ነው ያዳነን፡፡

    በተጨማሪ በ1ጴጥሮስ 2፡24 ላይ የሚከተለውን እናነባለን፡- ‹‹ለኃጢአት ሞተን ለጽድቅ እንድንኖር፥ እርሱ ራሱ በሥጋው ኃጢአታችንን በእንጨት ላይ ተሸከመ››፡፡ በእግዚአብሔር ፊት ጻድቃን ሆነን አንድንታይ ክርስቶስ የኃጢአታችንን እዳ መክፈል ነበረበት፡፡ ሰው በዚህ መንገድ ጻድቅ ሆኖ በእግዚአብሔር ዘንድ ሲታይ እግዚአብሔር ያዘጋጀውን የድነት ስጦታ ተቀብሏልና ከዘላለም ፍርድ ይድናል፡፡

    የመስቀል ሞት የሰው ልጅ ሰውን አሰቃይቶ ለመግደል ካበጃቸው የስቃይ ፍርዶች አሰቃቂው ነው፡፡ ከዚህ የባሰ የለም፡፡ ጌታችን በዚህ መስቀል ላይ መግለጽ በሚያስቸግር ስቃይና ጣር ለስድስት ሰአታት ቆየ፡፡ እግዚአብሔር እኛን በማዳን ስራ ውስጥ ጻድቅ ይሆን ዘንድ ቅጣታችንን በመቀበል ስለእኛ ሞተ፡፡ ምን አይነት ፍቅር ነው! እርሶና እኔ ቃሉን ለመታዘዝ ክርስቶስ የከፈለው ዋጋ በቂ ምክኒያታችን አይሆንምን? ስለዚህ የሃጢያታችንን ዋጋ ተቀብሎ የሞተልንን ጌታ አሁን በልባችን አምነን ብንቀበል የዘላለምን ህይወት እናገኛለን። ሌላ ደግሞ ከዚህ ቀጥሎ የእግዚአብሄር ልጅ የመባልን ስልጣን ያገኘንበትም ስለሆነ በቀጣዩ ክፍል እንገናኝ። ቸር እንሰንብት።

    ካሱ ቦስተን

  • የዘላለም ህይወት እንዳለን እርግጠኛ ነን ?

    ክፍል 4

    የእግዚአብሄር መፍትሄ

    ባለፈው ክፍል 3 ላይ የሃጢያት መዘዙን አይተናል በዛሬው ክፍል 4 ላይ  ለሰው ልጆች  የኃጢአት ችግር እግዚአብሔር መፍትሄ ያዘጋጀበትን እውነት እናያለን፡፡ እግዚአብሔር የፍቅር አምላክ ነው፡፡ ዮሐንስ 3፡16፣ ‹‹በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና››፡፡ ነፍስን ለሌላው አሳልፎ ከመስጠት የሚበልጥ ፍቅር ምን ሊሆን ይችላል?

    እግዚአብሔር ፍቅር ብቻ ሳይሆን ጻድቅ ፈራጅም ነው፡፡ ዮሐንስ 5፡30፣ ‹‹እኔ ከራሴ አንዳች ላደርግ አይቻለኝም፤ እንደ ሰማሁ እፈርዳለሁ ፍርዴም ቅን ነው፣ የላከኝን ፈቃድ እንጂ ፈቃዴን አልሻምና››፡፡ ፍትህ በኃጥኡ ላይ ይፈርዳል፡፡ ለአብነት የሚከተለውን እንመልከት፡- ባንክ ስዘርፍ ተገኝቼ ለፍርድ ወዳጄ የሆነ ዳኛ ፊት ቀረብኩ እንበል፡፡ ይህ ዳኛ ወደእርሱ ከጠራኝ በኋላ የክስ ወረቀትህን እቀደዋለሁ፤ ከአሁን ጀምሮ ከፍርድ ነጻ ነህ፤ ውጣ፤ ቢለኝ፣ ጻድቅ ፈራጅ ያሰኘዋል? ፈጽሞ! እግዚአብሔር ጻድቅ ፈራጅ ነው፡፡

    አግዚአብሔር ሕግ ሰጠ፣ የሰው ልጅ ተላለፈው፣ ፈጣሪም የጽድቅ ፍርድ አስተላለፈ፡፡ ይህም ፍርድ ሞት ይባላል፡፡ የሰው ልጅ በሞት ፍርሃት ውስጥ እየማቀቀ ለበርካታ አመታት በምድር ላይ የስቃይ ኑሮ መግፋት ጀመረ፡፡

    ይህን ፍርድ ያስተላለፈው አምላክ ጻድቅ ብቻ ሳይሆን የፍቅር አምላክ በመሆኑ፣ ከእስትንፋሱ የተካፈለው ሰው በምድር ላይ ሲሰቃይ ማየት አላስቻለውም፡፡ በዚህም ምክኒያት ጻድቅ ፈራጅነቱንና የፍቅር አምላክነቱን አዋህዶ የሚያሳይ ሌላ የድነት መንገድ ለሰው ልጅ አዘጋጀ፤ ይህ የድነት መንገድ ጽንፍ የሚመስሉትን የአምላክ ሁለት ባሕሪያት (ፍርድና ምሕረት) በአንድ መስመር ያገናኘ አስገራሚ ክስተት ነበር፡፡ እግዚአብሔር በሰው ዘር ሁሉ ላይ ያሳለፈው ሊታጠፍ የማይችል የሞት ፍርድ ሳይቀለበስ የሰው ልጅ ከተቆጣው አምላኩ ጋር ታረቀ፡፡ የአገራችን የእምነት ሊቃውንት ይህንን ሁኔታ ግሩም በሆነ መንገድ እንዲህ በማለት ይገልጹታል፡፡ “እግዚአብሔር ሰውን ከፈጠረበት ጥበቡ ይልቅ ያዳነበት ጥበቡ ተጠበበች፡፡” የዚህ አስገራሚ ትእይንት ጀማሪና ፈጻሚው ደግሞ ምንም በደል ያልተገኘበት ኢየሱስ ነበር፡፡ እግዚአብሔር በሰው ልጅ ላይ የተቆጣውን ቁጣ በኢየሱስ ላይ አሳረፈው፤ ፍርዱን አሳየ፡፡ ኢየሱስ ስለ ኃጢአተኞቹ ስለ እኛ ሞተ፡፡ በእርሱም ምክኒያት የሰው ልጅ ምኅረትን ተቀበለ፡፡ ከፈጣሪውም የፍርድ ቁጣ ተረፈ ‹‹ይልቁንስ እንግዲህ አሁን በደሙ ከጸደቅን በእርሱ ከቍጣው እንድናለን›› (ሮሜ. 5፡9)፡፡

    እግዚአብሔር የፍቅር አምላክ ብቻ ሳይሆን የበቀል አምላክም ጭምር ነው፡፡ ዕብራዊያን 10፡30-31 እነዲህ ይላል፡- ‹‹በቀል የእኔ ነው፣ እኔ ብድራትን እመልሳለሁ ያለውን እናውቃለንና፤ ደግሞም። ጌታ በሕዝቡ ይፈርዳል። በሕያው እግዚአብሔር እጅ መውደቅ የሚያስፈራ ነው››፡፡ ብዙ ሰዎች እግዚአብሔርን በፍቅር አምላክነቱ ብቻ ማወቅ ይሻሉ፡፡ ይህ ግን ስህተት ነው፡፡ በፍርድ ቀን ሁሉ ሰው በእግዚአብሔር እጅ መውደቅ እንዴት ያለ አስፈሪ ነገር እንደሆነ ያውቃሉ፡፡

    ኢየሱስ መሞት ለምን አስፈለገው? ምክኒያቱም እግዚአብሔር የፍቅር አምላክ ብቻ ሳይሆን ጻድቅ ፈራጅም ጭምር ስለሆነ፡፡ ፍትህ ከፍርድ ውጪ ሊታሰብ አይችልም፡፡ እግዚአብሔር በመጽሐፍ ቅዱስ የኃጥኡን ኃጢአት እንዴት እነደሚያነጻ ገልጿል፡፡ ለኃጢአታችን መንጻት ይህንን መንገድ ልንከተል ይገባል፡፡ ዛሬም ኩነኔ ያለባቸው ሁሉ ይህን የእግዚአብሔር መንገድ ያልተከተሉቱ ብቻ ናቸው፡፡ እነዚህም ክርስቶስ ዳግም ሲመጣ የሚሆንባቸውን 2ተሰሎንቄ 1፡8-10 እንዲህ በማለት ይገልጽልናል፡- ‹‹እግዚአብሔርን የማያውቁትን፣ ለጌታችንም ለኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል የማይታዘዙትን ይበቀላል፤ በዚያም ቀን በቅዱሳኑ ሊከብር፣ ምስክርነታችንንም አምናችኋልና በሚያምኑት ሁሉ ዘንድ ሊገረም ሲመጣ፥ ከጌታ ፊት ከኃይሉም ክብር ርቀው በዘላለም ጥፋት ይቀጣሉ››፡፡

    እግዚአብሔር የጸጋ አምላክም ጭምር ነው፡፡ ጸጋ ለማይገባቸው ሰዎች የተሰጠች የእግዚአብሔር ነጻ ስጦታ ነች፡፡ ሮሜ 3፡23-24 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል››፡፡ ሁላችን ኃጢአትን አድርገናል፡፡ በዚህም ምክኒያት ሁላችን የገሃነም ፍርድ ይገባናል፡፡ ሆኖም ግን እግዚአብሔር በማይገባን ስጦታ (በጸጋ) ማለትም በክርስቶስ ቤዛነት እኛን ሊያድን ወደደ፡፡ ቤዛነታችን ክርስቶስ ነው፡፡ሰው የሚድነው በጸጋው ነው፡፡ በኤፌሶን 2፡8-9 ላይ እንዲህ እናነባለን፡- ‹‹ጸጋው በእምነት አድኖአችኋልና፤ ይህም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው እንጂ ከእናንተ አይደለም፤ ማንም እንዳይመካ ከሥራ አይደለም››፡፡ ‹‹በእምነት መታዘዝ›› (ሮሜ 16፡26) በኩል በጸጋ እንድናለን፡፡ ማንም በመልካምነቱ ወደ መንግስተ ሰማይ የመግባት ድፍረት የለውም፤ ምክኒያቱም ሁሉ ኃጢአትን አድርገዋልና፡፡ በጎነታችን ድነታችንን አይገዛልንም፡፡ ድነታችንን ለማግኘት የሚያስችል ፍጹም ሥራ ልንሰራ አንችልም፡፡ ኢሳይያስ 64፡6 ይመልከቱ፡- ‹‹ሁላችን እንደ ርኩስ ሰው ሆነናል፥ ጽድቃችንም ሁሉ እንደ መርገም ጨርቅ ነው፤ ሁላችንም እንደ ቅጠል ረግፈናል፥ በደላችንም እንደ ነፋስ ወስዶናል››፡፡ በማናችንም ውስጥ ለመዳን የሚሆን ምክኒያት አልተገኘብንም፡፡ ሁላችንን የሚያድነን የተገለጠው የእግዚአብሔር ጸጋ ብቻ ነው፡፡ ይህ የግዚአብሄር ጸጋ እንዴት ነው ያዳነን ? ቀጣዩን በሚቀጥለው ክፍል እናያለን እስከዚያው ቸር እንሰንብት።

    ይህንን መልእክት አንብበው ሲጨርሱ ከታች ያለውን ላይክ የሚለውን ከተጫኑ በኋላ ፎሎው የሚለውን ቢነኩ ቀጣዩ ክፍል ሲለቀቅ ወዲያው ያገኛሉ፤ ሃሳብ አስተያየትዎ አይለየኝ፤ ስለሚከታተሉ አመሰግንዎታለሁ።

    ካሱ ቦስተን

  • የዘላለም ህይወት እንዳለን እርግጠኛ ነን ?

    ክፍል 3

    ኃጢአትና መዘዙ

    ባለፈው ክፍል 3 ጽሁፌ ላይ የእግዚአብሄርን የማስጠንቀቂያ ሃሳብ አስፍሬ እንዳነበባችሁት እርግጠኛ ነኝ፤ ካላነበቡት ግን ያንን አንብበው ወደዚህ ክፍል እንዲሻገሩ እጠይቅዎታለሁ። በዛሬው ጽሁፌ ኃጢአት ያመጣብንን መዘዝ እና እንዴት ከእግዚአብሔር እንደለየን እንመለከታለን፡፡ 

    ኃጢአት ከእግዚአብሄር እንዴት እንደለየን መጽሃፍ ቅዱስ በኢሳይያስ 59፡2፣ ‹‹ነገር ግን በደላችሁ በእናንተና በአምላካችሁ መካከል ለይታለች፥ እንዳይሰማም ኃጢአታችሁ ፊቱን ከእናንተ ሰውሮታል››፡፡ ብሎ ይነግራናል፤ ከእግዚአብሔር የለየን ኃጢአት ነው፡፡ ሮሜ 3፡23 እንዲህ በማለትም ይህንን ሃሳብ ያጸናልናል ፡- ‹‹ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል››፡፡ በዚህ ምድር ላይ ከኖረ ሰው ኃጢአት ያልሰራ ጌታችን ኢየሱስ ብቻ ነው፡፡ ስለዚህ ሁላችን ድነት ያስፈልገናል፡፡ 1ዮሐንስ 1፡8 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ኃጢአት የለብንም ብንል ራሳችንን እናስታለን፥ እውነትም በእኛ ውስጥ የለም››፡፡ ሰው እራሱን በማሳት የኃጢአት ችግር የለብኝም ሊል ይችላል፡፡ ይህንን ሲል ግን ምን እያለ እንደሆነ 1ዮሐንስ 1፡10 ያሳየናል፡- ‹‹ኃጢአትን አላደረግንም ብንል ሐሰተኛ እናደርገዋለን ቃሉም በእኛ ውስጥ የለም››፡፡ እግዚአብሔር፡- ሁሉ ኃጢአት ሰርተዋል ሲል ሁሉም ሰርተዋል ማለት ነው፤ ያ ማለት እኔ አንተ አንቺ ሁላችንም ማለት ነው፡፡ ኃጢአት ከሰራን ይህ የሰራነው ኃጢአት ያስከተለብን መዘዝ አለ። 

    ሮሜ 6፡23 የኃጢአት መዘዝ ምን እንደሆነ ይነግረናል፡- ‹‹የኃጢአት ደመወዝ ሞት ነውና፤ የእግዚአብሔር የጸጋ ስጦታ ግን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን የዘላለም ሕይወት ነው›››፡፡ ሞት መለየት ማለት ነው፡፡ በአካል ስንሞት አካላችን በመቃብር ጉድጓድ ውስጥ ሲቀር ነፍሳችን ግን ወደሰራት አምላክ ትሄዳለች፡፡ የመክብብ መጽሐፍ 12፡7 እንዲህ ይላል፡- ‹‹አፈርም ወደ ነበረበት ምድር ሳይመለስ፥ ነፍስም ወደ ሰጠው ወደ እግዚአብሔር ሳይመለስ ፈጣሪህን አስብ››፡፡ በአካላዊ ሞት ነፍስ ከስጋ ትለያለች፡፡ ይህች ነፍስ ታዲያ ወደፈጣሪዋ ስትመለስ በምድር ላይ በስጋ ውስጥ በነበረችበት ወቅት በሰራችው ኃጢአት ምክኒያት የዘላለም መኖሪያዋን አዘጋጅታ ነውና የመጣችው ወደዚያው ወደዘላለም መኖሪያዋ ትጓዛለች። በክፍል ሁለት ላይ ወደ ዘላለም መኖሪያ የሚያደርሱ ሁለት መንገዶች እንዳሉና አንዱ ወደ ገሃነም (ወደ ዘላለም ሞት) አንዱ ደግሞ ወደ መንግስተ ሰማይ (ወደዘላለም ህይወት) የሚያደርስ እንደሆነ ሁለቱም ደግሞ ወደሚሄዱበት ስፍራ ላይ ለዘላለም እንደሚኖሩ ልዩነቱ ግን አንዱ ገሃነም አንዱ መንግስተ ሰማይ መሆኑን አይተናል። ሲዖል ሁሌም የእሳት ባህር ያለበት ስፍራ እንደሆነና የሁለተኛው ሞት ያገኛቸው ነፍሳት የሚሄዱበትን ስፍራ መጽሃፍ ቅዱስ በራዕይ 20 ላይ ይገልጽልናል።        

    በሮሜ 6፡23 ላይ ‹‹የኃጢአት ደመወዝ ሞት ነውና፤ የእግዚአብሔር የጸጋ ስጦታ ግን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን የዘላለም ሕይወት ነው››፡፡ እንደሚል አይተናል፡፡ ይህ ሞት ግን መንፈሳዊ ሞት ነው፡፡ ይህም ለዘላለም ከእግዚአብሔር መለየት ማለት ነው፡፡ ከእግዚአብሔር የተለዩ ሰዎች አድራሻቸው ገሃነም ይባላል፣ ራዕይ 21፡8፡- ‹‹ዳሩ ግን የሚፈሩና የማያምኑ የርኵሳንም የነፍሰ ገዳዮችም የሴሰኛዎችም የአስማተኛዎችም ጣዖትንም የሚያመልኩ የሐሰተኛዎችም ሁሉ ዕድላቸው በዲንና በእሳት በሚቃጠል ባሕር ነው፤ ይኸውም ሁለተኛው ሞት ነው››፡፡ ይህ ሁለተኛ ሞት ለዘላለም ከእግዚአብሔር ተለይቶ መኖር ማለት ነው፡፡

    ታዲያ ከዚህ ለዘላለም ከእግዚአብሄር የተለየነውን ወደ እግዚአብሄር እንድንቀርብ መፍትሄው ምንድነው ? ይህንን ጥያቄ ክፍል 4 ላይ እንመለከተዋለን እስከዚያው ቸር እንሰንብት።

    ጽሁፉን አንብበው ላይክ የሚለውን ከተጫኑ እና ፎሎው ካደረጉ አዳዲስ ጽሁፎች ሲለጠፉ ወዲያውኑ ያገኛሉ፤ ለሌሎችም ማካፈል አይርሱ። 

    ሃሳብ አስተያየት እንዲሁም ጥያቄ ካለዎት በአስተያየት መስጫው ላይ ያስፍሩ አመሰግናለሁ። 

    ካሱ ቦስተን

  • የዘላለም ሕይወት እንዳለን እርግጠኛ ነን ?

    ክፍል 2

    የእግዚአብሔር ማስጠንቀቂያ !

    የዘላለም ህይወት እንዳለን እርግጠኛ ነን ? በሚለው ርዕስ ስር 10 ክፍሎች ያሉትን የመጀመሪያውን ክፍል 1 ን አግኝተው እንዳነበቡ እርግጠኛ ነኝ ካላነበብቡት ግን ይህንን ጽሁፍ ከማንበብዎ አስቀድመው የክፍል 1 ሃሳብን አንብበው ይህንን ክፍል 2 ን እንዲቀጥሉ ከአደራ ጋር እጠይቅዎታለሁ። በዛሬው ጽሁፌ ላይ የእግዚአብሄር ማስጠንቀቂያ የሆነውን ሃሳብ ከመጽሃፍ ቅዱሳችን ላይ እንመልከት፦

    ሁሉን የሚያውቅ አምላካችን ክርስቶስ በፍርድ ቀን ብዙዎች እንደሚጠፉና ጥቂቶች ብቻ እንደሚድኑ አስረግጦ ነግሮናል፡፡ ማቴዎስ 7፡13-14 እንዲህ ይላል፡- ‹በጠበበው ደጅ ግቡ፤ ወደ ጥፋት የሚወስደው ደጅ ሰፊ፣ መንገዱም ትልቅ ነውና ወደ እርሱም የሚገቡ ብዙዎች ናቸው›፡፡ ይህ ጉዳይ ትኩረታችንን ሊስብ የሚገባ ነገር ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ መሰረት በርካቶቹ የአለማችን ሕዝቦች መንግስተ ሰማይን አይወርሱም፡፡ እነዚህ ሰዎች በሰፊው ጎዳና ወደዘላለም ጥፋት የሚሄዱ ናቸው፡፡ ይህንን ማስጠንቀቂያ ያለማመቻመች ልንቀበለው ይገባል፡፡ ጌታ ኢየሱስ እንዳለው የሚድኑት ጥቂቶች ናቸው፡፡

    ለመሆኑ ጥቂት ሲባል ምን ያህል ነው? በ 1ጴጥሮስ 3፡20 ላይ እንዲህ ተጽፏል፡- ‹‹ጥቂቶች ማለት ስምንት ነፍስ በውኃ የዳኑበት መርከብ ሲዘጋጅ፣ የእግዚአብሔር ትዕግሥት በኖኅ ዘመን በቈየ ጊዜ ቀድሞ አልታዘዙም››፡፡ በኖኅ ዘመን ምድራችን ላይ እስከ ሁለት መቶ ሚሊዮን ሰዎች ይኖሩ እንደነበር ይገመታል፡፡ ነገር ግን ከእነዚህ ሰዎች መካከል ከጥፋት ውሃ መትረፍ የቻሉት ስምንት ሰዎች ብቻ ነበሩ፡፡ይህ አስደሳች ቁጥር አይደለም፡፡ ምንም እንኳን መጽሐፍ ቅዱስ በ 2ጴጥሮስ 3፡9 ላይ ‹‹ለአንዳንዶች የሚዘገይ እንደሚመስላቸው ጌታ ስለ ተስፋ ቃሉ አይዘገይም፣ ነገር ግን ሁሉ ወደ ንስሐ እንዲደርሱ እንጂ ማንም እንዳይጠፋ ወዶ ስለ እናንተ ይታገሣል›› ቢልም፣ ጌታ ኢየሱስ በማቴዎስ 7፡13-14 ላይ ስለዘላለም ሕይወት ሲናገር ድነት የሚያገኙት ጥቂቶች ብቻ እንደሆኑ ይናገራል ‹‹በጠበበው ደጅ ግቡ፤ ወደ ጥፋት የሚወስደው ደጅ ሰፊ፥ መንገዱም ትልቅ ነውና፥ ወደ እርሱም የሚገቡ ብዙዎች ናቸው››፡፡ የተቀሩት በርካታዎቹ፣ የዘላለም ሕይወታቸውን እሳቱ በማይጠፋበት ገሀነም ያጠፋሉ፡፡

    ወደ ዘላለም ሕይወት የሚያደርሱ ሁለት መንገዶች አሉ፡፡ ከእነዚህ መካከል አንዱ ብቻ ወደ መንግስተ ሰማይ ያደርሰናል፡፡ እኛ የሰው ልጆች በአሁኑ ሰአት ከሁለቱ በአንዱ መንገድ ላይ እንገኛለን፡፡ አንድ ነገር ልጠይቅዎትና እርሶ በየትኛው መንገድ ላይ እንዳሉ ያውቃሉ? ምርጫው የእርሶ ነው፡፡ ነጻ ፈቃድ አሎት፡፡ ከእንስሳት ከሚለይዎት ነገሮች መካከል አንዱ ይህ ነጻ ፈቃድዎ ነው፡፡

    እግዚአብሔር ማንም እንዳይጠፋ የሚፈልግ ቢሆንም፣ ምርጫውን ግን ለእኛ ሰጥቷል፡፡ 2ጴጥሮስ 3፡9 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ለአንዳንዶች የሚዘገይ እንደሚመስላቸው ጌታ ስለ ተስፋ ቃሉ አይዘገይም፥ ነገር ግን ሁሉ ወደ ንስሐ እንዲደርሱ እንጂ ማንም እንዳይጠፋ ወዶ ስለ እናንተ ይታገሣል››፡፡  1ጢሞቴዎስ 2፡4 ስለ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሰዎች ሁሉ ሊድኑና እውነቱን ወደ ማወቅ ሊደርሱ በሚወድ በእግዚአብሔር በመድኃኒታችን ፊት መልካምና ደስ የሚያሰኝ ይህ ነው››፡፡ እንግዳው ለመዳን በእጃችን ላይ ያለውን ውሳኔ እንጠቀም፡፡ድነትን ለማግኘት ስለ ድነት ትክክለኛ እውቀት ሊኖረን ይገባል፡፡ ኢየሱስ እንዲህ አለ፡- ‹‹እውነትንም ታውቃላችሁ እውነትም አርነት ያወጣችኋል አላቸው› የዮሐንስ ወንጌል 8፡32፡፡ ለመሆኑ አርነት የሚያወጣን እውነት ምንድን ነው? በዮሐንስ ወንጌል 17፡17 ላይ እንዲህ የሚል ቃል ሰፍሮ እናገኛለን፡- ‹‹በእውነትህ ቀድሳቸው፤ ቃልህ እውነት ነው››፡፡ ስለዚህ ወደ መንግስተ ሰማይ እንድንገባ አርነት የሚያወጣን እውነት ያለው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ብቻ ነው፡፡መቼም በቤትዎ መጽሃፍ ቅዱስ እንዳለና እያነበቡት እንዳለ እርግጠኛ ነኝ። ስለዚህ መጽሃፍ ቅዱስ ውስጥ ኃጢአት ምን እንደሆነና መዘዙን ሁሉ አስፍሮልናል። በሚቀጥለው ክፍል 3 ጽሁፌ ላይ ኃጢአት የሚያመጣቸውን መዘዞች ይዤልዎት እመጣለሁ እስከዚያው ሰላም ቆዩኝ፡፡

    ይህንን ጽሁፍ ካነበቡ በኋላ ለአንድ ወዳጅዎ ማካፈልዎትን አይርሱ አስተያየትና ጥያቄ ካለዎት በሃሳብ መስጫው ላይ ያስፍሩ፤ አመሰግንዎታለሁ።

    ካሱ ቦስተን

  • የዘላለም ሕይወት እንዳለን እርግጠኛ ነን ?

    ክፍል 1

    የዘላለም ሕይወታችን

    “የዘላለም ሕይወት እንዳለን እርግጠኛ ነን?” የሚለው ይህ ጽሁፍ 10 ክፍሎች አሉት፡፡ ለዛሬው ክፍል 1 ን ይዤ ቀርቤያለሁ፤ ማንኛውም ጥያቄ ሆነ አስተያየት ቢኖርዎ፣ በአስተያየት መስጫው ላይ ቢያሰፍሩ ተገቢውን ምላሽ ለመስጠት ቃል እገባለሁ፡፡

    በዚህ ጽሁፍ ውስጥ የቀረቡ ሃሳቦች የእኔን አስተሳሰብና ግምት የያዙ ሳይሆኑ በቀጥታ መጽሐፍ ቅዱስ የሚለውን የሚናገሩ ናቸው፡፡ መጽሐፍ ቅዱሱ ሲናገር ልንናገር፣ ዝም ሲል ደግሞ ዝም ልንል ግድ ነውና፡፡ የምናደርጋቸውን ነገሮች ሁሉ በመጽሐፍ ቅዱስ መሰረት ልናደርጋቸው፣ በጽሐፉ በስማቸው የሚጠራቸውንም በግልጽ ልንጠራቸው ይገባል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ከሚለው ያነሰ፣ የበዛ፣ ወይም የተለየ ነገር ሁሉ የስህተት ትምህርት ነውና፡፡

    ከእግዚአብሔር ቃል እውቀት ማነስ የተነሳ በተፈጠሩት በርካታ ሃይማኖቶች ምክኒያት በአለም ሕዝቦች መካከል ከፍተኛ ግራ በጋባት ይስተዋላል፡፡ በአሁኑ ሰአት በአለማችን ላይ የተለያየ አስተምህሮዎች፣ የስነ መለኮት ምልከታዎች እና አስተሳሰቦች ያልዋቸው ከ 600 በላይ ቤተ እምነቶች ይገኛሉ፡፡ በእነዚህ በርካታ እምነቶች ‹የእመን› ጥያቄ የሚቀርብላቸው የአለማችን ሰዎች ምን እና ማንን ማመን እንዳለባቸው ለመወሰን ግራ ተጋብተዋል፡፡ አዳኛችን የሆነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ በፈቃዱ በከፈለው ስቃይና ሞት ለኃጢአታችን ይቅርታ የሚያስፈልገውን ሁሉ አቅርቦልናል፡፡ በፍርድ ቀን ከሰይጣንና ከመላእክቱ ጋር ወደ ወደ ዘላለም እቶን እሳት መጣል አይገባንም፡፡ እናም ለመዳን የወንጌልን እውነት መታዘዝ ይኖርብናል፡፡ ወንጌል ምንድን ነው? ለመዳን ምን ማድረግ ይኖርብናል? በዚህ ጽሁፍ ውስጥ እግዚአብሔር በሰማይ ያዘጋጀልንን የዘላለም ሕይወት ስጦታ ለመውረስ መጽሐፍ ቅዱስ ምን ማድረግ እንዳለብን የሚናገረውን አብረን እናነባለን፡፡

    ከመጽሐፍ ቅዱስ የተወሰዱ ጥቅሶች በሙሉ ጠመም/ዘመም ባለ የፊደል አጻጻፍና ደማቅ ሆነው የቀረቡ ሲሆን ለእነዚህ ጥቅሶች ልብዎንና አእምሮዎን ሊከፍቱ ይገባል፡፡ እግዚአብሔር በእነዚህ ቃሎች ውስጥ ምን ሊያስተላልፍ እንደፈለገ መግለጥ የዚህ ጽሁፍ ዋነኛ አላማ ነው፡፡ ከመጽሐፍ ቅዱስ የተወሰዱትን እነዚህን ጥቅሶችን ሲያነቡ ለተሰመረባቸው ቃላት ልዩ ትኩረት እንዲሰጡ እጠይቅዎታለሁ፡፡

    የዘላለም ሕይወት ስለማግኘትዎ እርግጠኛ ነዎት? ይህ ጥያቄ የዘላለም ሕይወትን በተመለከተ ዋነኛ ጥያቄያችን መሆን አለበት፡፡ ዛሬ ብንሞት በእርግጠኝነት በቀጥታ ወደ ገነት እንደምንሄድ እናውቃለን? ነፍሳችን ከስጋችን ከተለየች በኋላ ይህን የምርጫ እድል ዳግመኛ የማናገኝበት በመሆኑ ጥያቄውን በቸልታ ልናልፈው አይገባም፡፡ አንድ ቀን፣ ለዚህ ጥያቄ የሰጠነውን ምላሽ ለማወቅ ሁላችን በፍርድ ወንበር ፊት እንቀርባለን፡፡ የሰው ልጅ ሊያስቀራቸው የማይችላቸው ሁለት ነገሮች ከፊቱ ይጠብቁታል፡፡ እነዚህ ነገሮች ሞትና ፍርድ ይሰኛሉ፡፡ ‹‹ለሰዎችም አንድ ጊዜ መሞት ከእርሱ በኋላም ፍርድ እንደ ተመደበባቸው፣›› ዕብራዊያን 9፡27፡፡ ማንም ሰው እነዚህን ነገሮች ሊያመልጥ አይችልም፡፡

    ማንም ሰው ስለነገው ቀርቶ ከጥቂት ሰከንዶች በኋላ ስለሚሆነው ነገር እርግጠኛ ሊሆን አይችልም፡፡ ስለዚህ በምንም መንገድ ይህን ጥያቄ ለነገ ልንገፋው አይገባንም፡፡ እግዚአብሔር በያዕቆብ መልእክት 4፡14 ላይ እንዲህ ሲል ያስጠነቅቀናል፡- ‹‹…ነገ የሚሆነውን አታውቁምና። ሕይወታችሁ ምንድር ነው? ጥቂት ጊዜ ታይቶ ኋላ እንደሚጠፋ እንፍዋለት ናችሁና።››

    ለእኛ አእምሮ ‹‹ትክክል›› እና ‹‹ስህተት›› በሚመስሉን መመዘኛዎች ላይ ተመስርተን የዘላለም ሕይወትን በሚያህል ውድ ነገር ላይ ስህተት መስራት የለብንም፡፡ ለዚህ ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት በስሜቶቻችንም ላይ ቢሆን መመስረት የለብንም፡፡ እስቲ መጽሐፍ ቅዱስ በምሳሌ 14፡12 ላይ የሚለውን እንመልከት፡- ‹‹ለሰው ቅን የምትመስል መንገድ አለች ፍጻሜዋ ግን የሞት መንገድ ነው››፡፡ ለውሳኔዎቻችን ትክክለኛነት ማረጋገጫው መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ መሆን ይገባዋል፡፡

    ደኅንነታችንን (ድነታችንን) በተመለከተ የግል ግምቶቻችን ምንድን ናቸው? እኛ የምናቀርባቸው ብዙዎቹ ግምቶች እግዚአብሔር በቃሉ ካስቀመጠው እውነታ ጋር የሚቃረኑ ናቸው፡፡ ስለዚህ ያሉንን ግምቶች ሁሉ በእግዚአብሔር ቃል መፈተሸ ይኖርብናል፡፡ ይህንን በምናደርግበት ወቅት በእኛና በእግዚአብሔር ቃል መካከል ያሉ በርካታ ልዩነቶችን ማስተዋል እንጀምራለን፡፡ ጌታችን በማርቆስ 7፡7 እንዲህ ይላል፡- ‹‹የሰውም ሥርዓት የሆነ ትምህርት እያስተማሩ በከንቱ ያመልኩኛል ተብሎ እንደ ተጻፈ በእውነት ትንቢት ተናገረ››፡፡ አምልኮአችን በእግዚአብሔር ቃል ላይ ያልተመሰረተ ሲሆን ከንቱ ይሆናል። የእነዚህ ሁሉ አደናጋሪ ትምህርቶች ምንጭ እግዚአብሔር ይመስሎታል? ፈጽሞ! 1ቆሮንቶስ 14፡33 እንዲህ ይላል፡- ‹‹እግዚአብሔርስ የሰላም አምላክ ነው እንጂ የሁከት አምላክ አይደለምና፤ በቅዱሳንም አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ እንዲህ ነው››፡፡ ሐዋሪያው ጴጥሮስ ለአይሁድ ሸንጎ በሐዋሪያት ሥራ 5፡29 ላይ እንዲህ ብሎ ተናገረ፡- ‹‹ከሰው ይልቅ ለእግዚአብሔር ልንታዘዝ ይገባል››፡፡

    በመጨረሻው ዘመን የሰውም ሆነ የእኛ አስተያየት ከፍርድ ለማምለጥ ምክኒያት አይሆኑንም፡፡ ከፍርድ የሚያስመልጠን በእግዚአብሔር ቃል መሰረት ያመነው ነገር ብቻ ነው፡፡ ጌታ ኢየሱስ፣ ስለ ዘላለም ሕይወት አስመልክቶ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ በነገረን እውነት አንጻር የምንዳኝበት የፍርድ ቀን ይመጣል፡፡ ፍርድ የሚሰጠው በዚህ መመዘኛ ብቻ ነው፤ ምክኒያቱም ጌታችንና መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲህ ብሎ ተናግሯልና፣ የዮሐንስ ወንጌል 12፡48 ‹‹በማይቀበለኝና ቃሌን በሚያቃልል ላይ የሚፈርድበት አለ፤ የተናገርሁት ቃል ራሱ በመጨረሻው ቀን ይፈርድበታል››፡፡ (ከአዲሱ መደበኛ ትርጉም መ/ቅ የተወሰደ) ስለዚህ የዘላለም ሕይወትን አስመልክቶ ማንም ሰው የመጽሐፍ ቅዱስ ማስረጃ በሌለበት የግሉን አስተያየት ቢሰጠን ልንቃወም ይገባል፡፡ ከነፍሳችን በላይ ምን ሊያሳስበን የሚችል ነገር ይኖራል?

    የነፍሳችንን ዋጋ በአለም ያለ ምንም ነገር ሊመጥነው እንደማይችል ያውቃሉ? ማቴዎስ 16፡26 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሰው ዓለምን ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱን ግን ቢያጣ ምን ይጠቅመዋል? ወይስ ሰው በነፍሱ ምትክ ሊከፍለው የሚችለው ዋጋ ምንድነው?›› (ከአዲሱ መደበኛ ትርጉም መ/ቅ የተወሰደ) ነፍሳችን ዘላለማዊ ናት፡፡ እናም ይህችን ነፍስ ለዘላለም በእቶን እሳት ውስጥ እንድትኖር ሊያደርጋት የሚችሉ ጉዳዮችን ሁሉ በቸልታ መመልከት ፈጽሞ አይገባንም፡፡

    ክፍል 2 ን በሚቀጥለው ጽሁፌ ይዤልዎት እቀርባለሁ እስከዚያው ቸር እንሰንብት።

    ካሱ ቦስተን

  • መንፈሳዊ ትረካ

    የመጨረሻው ትንቅንቅ ቁጥር 2 መንፈሳዊ ትረካ የሚቀጥለው ቅዳሜ በ 2/19/22 ማለዳ ይቀርብላችኋል ቁጥር አንድ ትረካን “kassuboston” ብለው በስልክዎም ሆነ በኮምፒውተር ላይ ጎግል በማድረግ ዩቲዩብ ላይ ገብተው ማዳመጥ ይችላሉ አመሰግናለሁ
    ካሱ ቦስተን
  • ጋብቻ

    መጋባት በሁሉ ዘንድ ክቡር መኝታውም ንጹሕ ይሁን፤ ሴሰኞችንና አመንዝሮችን ግን እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል። (ወደ ዕብራውያን 13፥4)

        በመጀመሪያ ደረጃ እግዚአብሔር ጋብቻን በሁሉ ዘንድ ክቡር ይሁን ነው ያለው በሁሉ ዘንድ ሲል በሴቷም በወንዱም በእስልምናውም በክርስትናውም በማንኛውም የሰው ዘር ሊከበር ይገባዋል ነው የሚለው እንዲሁ እንደቀልድ የሚታይ ነገር አይደለም እንደቀልድ ዛሬ ተገብቶበት ነገ የሚወጣበት እንደዘበት የሚታይ ጉዳይ አይደለም ነው የሚለን ።

      ሌላው ደግሞ ጋብቻ በአንድ ወንድና በአንዲት ሴት መካከል (ይህ ሃሳብ ሊተኮርበት የሚገባው ነው) የሚፈጸም የመንፈስ የነፍስ እና የስጋ ጥምረት ያለበት ነው ይህም ጋብቻ በሁለት ተቃራኒ ጾታ መሃከል የሚፈጸም እና ዘለቄታ ያለው በእግዚአብሔር በቅዱሳን መላአክቱና እና  በሰው ፊት የሚደረግ የቃልኪዳን ትስስር ያለበት ስርዓት ነው ።   

      ዛሬ ዛሬ እንደምናየው ግን የጋብቻን ክቡርነት በዘነጉና ጋብቻ እንዴት እንደተጀመረ ባልተረዱ ግለሰቦችና የጋብቻ አስፈጻሚ ድርጅቶች እንዲሁም የሃይማኖት ድርጅቶች ውስጥ የሚፈጸመው ቅጥ ያጣ እና ስርዓት የሌለው ወንድና ወንድን እንዲሁም ሴትና ሴትን እያጣመሩ ጋብቻን የመሰረቱ የሚመስላቸው ግለሰቦችም ሆኑ ድርጅቶች በምድር ላይ ጥፋትን እንጂ መልካም የሆነን ስርዓት እየፈጽሙ ላለመሆናቸው ሊረዱት ይገባቸዋል። እነዚህን ግለሰቦች ደግሞ እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል ምክንያቱም የእግዚአብሔር ቃል እንዲህ ይላልና   ( … ወይስ ዓመፀኞች የእግዚአብሔርን መንግሥት እንዳይወርሱ አታውቁምን? አትሳቱ፤ ሴሰኞች ቢሆን ወይም ጣዖትን የሚያመልኩ ወይም አመንዝሮች ወይም ቀላጮች ወይም ከወንድ ጋር ዝሙት የሚሠሩ ወይም ሌቦች ወይም ገንዘብን የሚመኙ ወይም ሰካሮች ወይም ተሳዳቢዎች ወይም ነጣቂዎች የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም። 1 ቆሮ 6 : 9-10)

    ሴሰኞችንና አመንዝሮችን እግዚአብሔር ከፈረደባቸው ስርዓቱን እያስፈጸሙ ያሉትም ከዚህ ፍርድ የሚያመልጡበት መንገድ አይታየንም ስለዚህ ይህንን ስርዓት ከማስፈጸም ሊታቀቡ ይገባቸዋል አንላለን።

       ከዚህ የባሰው የጥፋቶች ሁሉ ጥፋት ደግሞ ይህንን ስርዓት መንግስት ስለፈቀደውና በሕግ ስለተደገፈ ብቻ እግዚአብሔር የፈቀደው ያህል በእግዚአብሔር እናምናለን የሚሉና እግዚአብሔርን እናገለግላለን የሚሉ ግለሰቦችና የሃይማኖት ድርጅቶች የተቃውሞ ድምጻቸውን ያለማሰማታችውና ዝም የማለታቸው ጉዳይ ስርዓቱን ተስማምተው መቀበላቸውን የሚያሳይ እንጂ ሌላ ምንም ሊሆን እንደማይችል እንገነዘባለን። ትንሽ ቆይቶም እነዚሁ ግለሰቦች ስርዓቱን ለመፈጸም ወይም ጋብቻን ለመፈጸም ወደቤተክርስቲያን ቢመጡ የሚሰጣቸው ምላሽ ምን ሊሆን እንደሚችል መዘንጋት የለብንም ምክንያቱም አስቀድመን የተቃውሞ ድምጻችንን አላሰማንምና ።

       ይህንን ስርዓት እያስፈጸሙ ያሉና ለማስፈጸም ችግር እንደሌለበትና የማያስጠይቃቸው የመሰላቸው ቤተአምልኮዎች ከእግዚአብሔር ሳይሆን ከአባታቸው ከዲያብሎስ ዘነድ የተላኩ የጥፋት መልእክተኞች መሆናቸውን መዘንጋት የለብንም ።

         ስለዚህ በማስጠንቀቅም ይህንን ልላችሁ እወዳለሁ ራሳችሁን ብትመረምሩና ከየት እንደወደቃችሁ ብታስቡና ንስሐ ብትገቡ የትሻለ ነው እላለሁ። በትያጥሮንም ወዳለው ወደ ቤተ ክርስቲያን መልአክ እንዲህ ብለህ ጻፍ፦ እንደ እሳት ነበልባል የሆኑ ዓይኖች ያሉት በእቶንም የነጠረ የጋለ ናስ የሚመስሉ እግሮች ያሉት የእግዚአብሔር ልጅ እንዲህ ይላል፦ ሥራህንና ፍቅርህን እምነትህንም አገልግሎትህንም ትዕግሥትህንም ከፊተኛውም ሥራህ ይልቅ የኋለኛው እንዲበዛ አውቃለሁ። ዳሩ ግን፦ ነቢይ ነኝ የምትለውን ባሪያዎቼንም እንዲሴስኑና ለጣዖት የታረደውን እንዲበሉ የምታስተምረውንና የምታስተውን ያችን ሴት ኤልዛቤልን ስለምትተዋት የምነቅፍብህ ነገር አለኝ፤ ንስሐም እንድትገባ ጊዜ ሰጠኋት ከዝሙትዋም ንስሐ እንድትገባ አልወደደችም። እነሆ፥ በአልጋ ላይ እጥላታለሁ፥ ከእርስዋም ጋር የሚያመነዝሩትን ከሥራዋ ንስሐ ባይገቡ በታላቅ መከራ እጥላቸዋለሁ ልጆችዋንም በሞት እገድላቸዋለሁ፤ አብያተ ክርስቲያናትም ሁሉ ኵላሊትንና ልብን የምመረምር እኔ እንደ ሆንሁ ያውቃሉ፥ ለእያንዳንዳችሁም እንደ ሥራችሁ እሰጣችኋለሁ። (ራእይ 2:18 – 23)

    ካሱ ቦስተን 

  • መንፈሳዊ ትረካ

    የመጨረሻው ትንቅንቅ መንፈሳዊ ትረካ ቁጥር 1 ቅዳሜ 02/12/22 ከማለዳው 7:30 ላይ ተለቋል ያዳምጡት ይጠቀሙበታል ይህ ትረካ 38 ክፍሎች አሉት ከቅዳሜ 2/12/22 ጀምሮ በየሳምንቱ ይቀርባል፡ የዩቲዩብ መስመራችንን “kassuboston” ብለው google ላይ ቢፈልጉት በቀላሉ ያገኙታል፤ ሰብስክራይብ የሚለውን ቢጫኑት ትረካውን በየሳምንቱ ማግኘት ይችላሉ። እናመሰግናለን።

    ካሱ ቦስተን