አንድ ቀን ከፈሪሳውያን አንዱ ኢየሱስን በቤቱ ምሳ እንዲበላ ለመነውና ወደ ቤቱ ገባ። «እነሆም በዚያች ከተማ ኃጢአተኛ የነበረች አንዲት ሴት፤ በፈሪሳዊው ቤት በማዕድ እንደ ተቀመጠ ባወቀች ጊዜ፥ ሽቱ የሞላበት የአልባስጥሮስ ቢልቃጥ አመጣች። በስተ ኋላውም በእግሩ አጠገብ ቆማ እያለቀሰች በእንባዋ እግሩን ታርስ ጀመረች፥ በራስ ጠጕርዋም ታብሰው እግሩንም ትስመው ሽቱም ትቀባው ነበረች።» (ሉቃ.7፡37-38) በዚህን ጊዜ ይህ ፈሪሳዊ በልቡ «ይህስ ነቢይ ቢሆን፥ ይህች የምትዳስሰው ሴት ማን እንደ ሆነች እንዴትስ እንደ ነበረች ባወቀ ነበር፥ ኃጢአተኛ ናትና ብሎ በልቡ አሰበ።» በማለት አሰበ። ኢየሱስም የልቡን ሐሳብ አወቀና እንዲህ ሲል በምሳሌ አስረዳው «ኢየሱስም መልሶ፦ ስምዖን ሆይ፥ የምነግርህ ነገር አለኝ አለው። እርሱም፦ መምህር ሆይ፥ ተናገር አለ። ለአንድ አበዳሪ ሁለት ተበዳሪዎች ነበሩት በአንዱ አምስት መቶ ዲናር ነበረበት በሁለተኛውም አምሳ። የሚከፍሉትም ቢያጡ ለሁለቱም ተወላቸው። እንግዲህ ከእነርሱ አብልጦ የሚወደው ማንኛው ነው? ስምዖንም መልሶ፦ ብዙ የተወለቱ ይመስለኛል አለ። እርሱም፦ በእውነት ፈረድህ አለው።ወደ ሴቲቱም ዘወር ብሎ ስምዖንን እንዲህ አለው፦ ይህችን ሴት ታያለህን? እኔ ወደ ቤትህ ገባሁ፥ ውኃ ስንኳ ለእግሬ አላቀረብህልኝም፤ እርስዋ ግን በእንባዋ እግሬን አራሰች በጠጕርዋም አበሰች። አንተ አልሳምኸኝም፤ እርስዋ ግን ከገባሁ ጀምራ እግሬን ከመሳም አላቋረጠችም። አንተ ራሴን ዘይት አልቀባኸኝም፤ እርስዋ ግን እግሬን ሽቱ ቀባች። ስለዚህ እልሃለሁ፥ እጅግ ወዳለችና ብዙ ያለው ኃጢአትዋ ተሰርዮላታል፤ ጥቂት ግን የሚሰረይለት ጥቂት ይወዳል። እርስዋንም። ኃጢአትሽ ተሰርዮልሻል አላት። (ሉቃ.7፡40-48)
በዚህ አስደናቂ ታሪክ ውስጥ ወደ ኢየሱስ የምንቀርብበት አቀራረብ ምን እንደሚመስል። የሰው ሐሳብና የእግዚአብሔር ሐሳብ ምን ያህል የተራራቀ እንደሆነ። አሁንም በዚህች ቅጽበት ወደ ጌታ እየቀረብንበት ያለውን መንገድ እንድንፈትሽ ለማየት እንችላለን።
ለመሆኑ በዚህ ስፍራ ካሉት ሁለት ኢየሱስን ተቀባዮች የትኛውን ትመስላለህ? ትመስያለሽ? ይህንን ጥያቄ ለመሆን የምንፈልገውን ከማሰብ አንጻር ሳይሆን አሁን ጌታን እያስተናገድንበት ካለው እውነተኛ ገጽታ አንጻር ብንመልሰው የበለጠ ተጠቃሚ እንሆናለን። መልሳችን መሆን ያለበት በውድድር እንዳለ ሰው ነጥብ ከማስቆጠር አንጻር ሳይሆን ከጌታ ጋር ያለንን ህብረት ፈትሸን ከማስተካከል አንጻር ይሁን።
እነዚህ ሰዎች ሁለቱም ወደ ጌታ ቀርበዋል ሁለቱም ጌታን ፈልገውታል። የፈለጉበት ልብና የቀረቡበት አቀራረብ ግን የተለየ ነው። ይህም በውጤቱ ላይ ለውጥ አምጥቶአል። እንደሰው ስናየው በአግባቡና በስርአቱ ያስተናገደውና የተቀበለው ፈሪሳዊው ነው። በክብር ምሳ ጋብዞታል። የጋበዘውም ወደ ሌላ ሰው ቤት ሳይሆን ወደራሱ ቤት ነው። ኃጢአተኛዋ ሴት ግን ይህን ሁሉ አላደረገችም። ኢየሱስ በፈሪሳዊው ቤት እንደተቀመጠ ባወቀች ጊዜ እንዲሁ ሳትጠራና ሳትጋበዝ መጣች። ይህ ፈሪሳዊ ለኢየሱስ እያደረገ ያለው የሚቆጠር የሚመካበት ነገር አለው። ይህች ሴት ግን ምንም የምትመካበትና የምትቆጥረው ነገር የላትም። ጌታን ወደቤትዋ አልጋበዘችውም (እንደሚመስለኝ በዝሙት የምትተዳደር ሴት ከሆነች ከዝቅተኛው ህብረተሰብ ስለምትመደብ ሰው የምትጋብዝበት ቤትም ያላት አይመስለኝም) ነገር ግን ራስዋን አዋርዳ ወዳልተጠራችበት ቤት ወዳልተጋበዘችበት ቤት መጣች። ለሰው ወዳልተጋበዙበት ግብዣ መሄድ የሚያሳፍር ነው። የሚገርመው ደግሞ የመጣችበት ቤት ለእንደርስዋ አይነት ሴት የማይሆን የፈሪሳዊ ቤት ነው። ይህ ፈሪሳዊ እርስዋን እንዴት እንደሚመለከታት ታውቃለች። ኃጢአተኛ ስለሆነች በህጉ አይን ነው የሚመለከታት። እንድትወገርና እንድትሞትም ሊያመቻች ይችላል። ስለዚህ ኢየሱስን አምና መጣች እንጂ እንደሰው ሲታይ ወደ ሞት ቀጠና ነው የመጣችው። ወንጀል ይዞ ፓሊስ ጣቢያ መሄድን ማን ይፈልግና። ወደዚህ ቤት እንድትመጣ ያስገደዳት ግን ከዚያ ከሚፈርድባትና እስከሞት ድረስ ከሚያሳድዳት በልጦ የነገሰው የዓለም ብርሃን ስለታያት ነው። «ብርሃንም በጨለማ ይበራል፥ ጨለማም አላሸነፈውም።» (ዮሐ.1፡5) ተብሎ እንደተጻፈ በዚያ ድሮ ሞትና ፍርድ ብቻ ነግሶ በሚታይበት የፈሪሳዊ ቤት ይህ ብርሃን አሸንፎ ታያት። ይህን ብርሃን ተማምና ወደዚያ ጨለማ መንደር ገባች።
ስለዚህ አቀባበላቸውን ስናይ የፈሪሳዊው ደረጃውን የጠበቀ ሲሆን የርስዋ ግን «ድንኳን ሰባሪ» እንደሚባሉት ህገ ወጥ የሚባል ነው። ይህ ፈሪሳዊ የሰራው ነገር ክፉ የሚባል ሳይሆን መልካም የሚባል ነው። ሌሎች ፈሪሳውያን ጌታን ለመግደል ሲያሳድዱትና በቃል ሊያጠምዱት ሲከታተሉት እርሱ ግን ወደ ቤቱ ጠርቶ ምሳ መጋበዙ ትንሽ ነገር አይደለም። ሌሎች ምን ይሉኛል አለማለቱም ያስመሰግነዋል። ኢየሱስን የጋበዘው ግን ማንነቱን አውቆ ሳይሆን ማንነቱን ለማወቅ እንደሆነ እናያለን። የተቀበለው አቀባበል ሰፍ ያለ ሰው አቀባበል አለመሆኑና ይህች ሴት በምትዳስሰው ጊዜ በልቡ ያሰበው ነገር ይህንን ፍንትው አድርጎ ያሳየናል። «ይህስ ነቢይ ቢሆን፥ ይህች የምትዳስሰው ሴት ማን እንደ ሆነች እንዴትስ እንደ ነበረች ባወቀ ነበር፥ ኃጢአተኛ ናትና ብሎ በልቡ አሰበ።» (ሉቃ.7፡39) ይላል። ስለዚህ ነቢይ ይሁን አይሁን ለመለየት ነበር የጠራው አሁን ማረጋገጫውን አገኘ ማለት ነው። እውነተኛው ረቢ ኢየሱስ ግን ባልጠበቀው መንገድ ሚስጢሩን ይተርክልት ጀመር። በእውነት ኢየሱስ እውነተኛ ረቢ ነው። ምሳ ተጋብዣለሁ ብሎ እውነትን የማይደብቅ ለራሱ ሊኖር ያልመጣ ከሰማይ የሆነ ሰው በመሆኑ በሰው ልጆች መንደር የተለመደው ምን ይሉኛል ያልነካካው። ለእውነት ሊመሰክር የተወለደ። ራሱ እውነት ሆኖ እውነትን ያስተማረ ድንቅ ረቢ።
«እግዚአብሔር ሕዝቤን ስለሚያስቱ ነቢያት እንዲህ ይላል በጥርሳቸው ሲነክሱ በሰላም ይሰብካሉ በአፋቸው ግን አንዳች በማይሰጥ ሰው ላይ ሰልፍን ያስቡበታል።» (ሚክ.3፡5) የተባለላቸው ሐሰተኞች በሞሉበት ዘመን ምሳ በልቶ እውነትን የሚናገርና የሚገሰጽ እውነተኛ እረኛ እግዚአብሔር ለህዝቡ ሰጠ። በዚህ ዘመን ያሉ «ስለ ጭብጥ ገብስና ስለ ቍራሽ እንጀራ» (ህዝ.13፡19) ህዝብን የሚያረክሱና ለሆዳቸውና ለኪሳቸው ያደሩ አገልጋዮች ከዚህ ድንቅ መምህር ፍለጋን ይማሩ ዘንድ ይገባል። ይህ ድንቅ መምህር በክብር ምሳ የጋበዘውን ሰው ወደ ቤቱ እንጂ ወደ ልቡና ወደ ህይወቱ እንዳልጋበዘው እንዲህ በማለት አስረዳው «ወደ ሴቲቱም ዘወር ብሎ ስምዖንን እንዲህ አለው፦ ይህችን ሴት ታያለህን? እኔ ወደ ቤትህ ገባሁ፥ ውኃ ስንኳ ለእግሬ አላቀረብህልኝም፤ እርስዋ ግን በእንባዋ እግሬን አራሰች በጠጕርዋም አበሰች። አንተ አልሳምኸኝም፤ እርስዋ ግን ከገባሁ ጀምራ እግሬን ከመሳም አላቋረጠችም። አንተ ራሴን ዘይት አልቀባኸኝም፤ እርስዋ ግን እግሬን ሽቱ ቀባች። (ሉቃ.7፡44-46) ዋው ይህ አክብሮ ምሳ ለጋበዘ ሰው እጅግ መራራ እውነት ነው። ግን እየመረረ የሚፈውስ መድኃኒት።
ዛሬም እንዲህ እላለሁ እግዚአብሔር ሆይ እየመረረንም ቢሆን እውነትን የሚነግሩንን እረኞችና አስተማሪዎችን አስነሳልን ይህ ይሻለናል።
አሜን ይሁንልን !!!
ካሱ ቦስተን
እባክዎን ካነበቡ በኋላ ላይክ የሚለውን ይጫኑ እንዲሁም መልእክቱን ለሌሎች ያካፍሉ አመሰግናለሁ