መሪና ተባባሪ

በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ከሚገኙ የመሪና የተባባሪ ድርሻን ከሚገልጡ ታሪኮች አንዱ የሙሴና፣ የአሮንና የሖር ታሪክ ነው(ዘጸ. 17÷8-16)፡፡

    አማሌቃውያን ከእስራኤል ጋር ሲዋጉ ኢያሱ ጎልማሶቹን ይዞ ከአማሌቃውያን ጋር ይዋጋ ነበር፡፡ ሙሴ ደግሞ ወደ ኮረብታው ወጣ፡፡ ሙዜ እጁን ባነሣ ጊዜ እስራኤል ድል ያደርጋሉ፡፡ ሙሴ ደክሞት እጁን ባወረደ ጊዜ ደግሞ አማሌቅ ድል ያደርጋሉ፡፡ በዚህ ሁኔታ ሙሴ ቀኑን ሙሉ ዋለ፡፡ በመጨረሻ ግን የሙሴ እጆች ከበዱ(ደከሙ)፡፡ ይህን የተመለከቱት አሮንና ሖር ለሙሴ የድንጋይ ወንበር አዘጋጁለት፤ ሙሴም እዚያ ድንጋይ ላይ ተቀምጦ እጁን ዘረጋ፡፡ ድሉም ለእስራኤል ሆነ፡፡ ነገር ግን አሁንም ሙሴ እጆቹ እየደከሙ መጡ፡፡ አሮንና ሖርም በግራና በቀኝ ሆነው የሙሴን እጆች ከፍ አድርገው ደገፏቸው፡፡ ያን ጊዜ ሙሴ እጆቹን አነሣ፡፡ እስራኤልም አማሌቅን ፈጽመው ድል አደረጉ፡፡

    አንድ መሪ ውጤታማ የሚሆው ብቻውን አይደለም፡፡ እንኳንና በሰዎች የተመረጠ መሪ እግዚአብሔር የመረጠው ሙሴ እንኳን ብቻውን ውጤታማ መሆን አልቻለም፡፡ መሪ ምን ጠቢብ፣ ጎበዝ፣ ውጤታማ፣ ተወዳጅና ዐቅም ያለው ቢሆንም እንኳን እንደ ሙሴ እጆች መዛሉ አይቀሬ ነው፡፡ ስለዚህም እንደ አሮንና እንደ ሖር መንገዱን አይቶ የሚደግፈው ይፈልጋል፡፡ መልካም መሪ ውሳኔዎቹ፣ የለውጥ ሐሳቦቹ፣ ዕቅዶቹና ቃል ኪዳኖቹ ተግባራዊ እንዲሆኑ የሚያበረቱት እንደ አሮንና ሖር የመሳሰሉ አጋዦች ያስፈልጉታል፡፡ አሮንና ሖር ለሙሴ የተሰጠው ሃላፊነት ወይም ራዕይ አልተሰጣቸውም፡፡ ነገር ግን ሙሴን ደግፈው የሚፈልጉትን ውጤት አመጡ፡፡ ሁሉም ሰው መሪ ባይሆንም የመልካም መሪን ሐሳብ፣ ዕቅድ፣ ራእይና ውሳኔ በመደገፍ ግን ለውጥ ማምጣት ይችላል፡፡

    ሙሴ አንድ ሲሆን ደጋፊዎቹ ግን ሁለት ነበሩ፡፡ ምንጊዜም ከደጋፊዎች ተደጋፊዎች ያንሳሉ፡፡ ታሪክ እንደሚያስተምረን ዓለምን የለወጧት ጥቂት ባለ ተሰጥዖዎች ናቸው፡፡ ነገር ግን ሐሳባቸውን፣ መንገዳቸውን፣ አመራራቸውን፣ ትምህርታቸውን፣ ጥረታቸውን የሚደግፉ አካላቶች ነበሯቸው፡፡  በቤተክርስቲያንም መርሁ አንድ ነው የቤተክርስቲያን መሪዎች እንዲሁም የየአገልግሎት ክፍል መሪዎች ሊደገፉ አይዞአችሁ ሊባሉ ከጎናችሁ ነን ሊባሉ ይገባቸዋል፡፡ መሪዎች ወይም ቤተክርስቲያንን ወደታየላት ግብ ለማድረስ ራዕይ ተቀብለው የሚንቀሳቀሱ ባለራዕዮች ስኬታማ የሚሆኑት የአገልግሎት ክፍሎች፣ በተለያየ ጸጋ የሚያገለግሉ አገልጋዮች፣ እንዲሁም ምዕመናን፣ ማግኘታቸው መሆኑን ልንዘነጋው አይገባንም፡፡

     ብዙ ሙሴዎች እንደ አሮንና ሖርን የመሰሉ አጋዦች አጥተው እጃቸው ዝሎ ድል ሆነዋል፡፡ መንገዱ፣ ሐሳቡ፣ ውጣ ውረዱ፣ ሙግቱ፣ ጭቅጭቁ፣ የሰው ትችትና ወቀሳ፣ ስድብና ዕንቅፋትነት አዝሏቸው ድል ከማድረግ ድል ወደመሆን ወርደዋል፡፡ በህይወት ዘመናችን ብዙ ሙሴዎች ተሰጥተውን ነበር፡፡ነገር ግን የሚያግዛቸውና ክንዶቻቸውን የሚደግፍ፤ ቢያንስ የድንጋይ መቀመጫ እንኳ የሚሰጥ አጥተው በሞትና በሽፈት ድል እየሆኑ ተገቢውን ለውጥ ሳያመጡ ቀርተዋል፡፡ ኧረ እንደውም ድንጋዩን እንዲቀመጡበት ከማድረግ ይልቅ ድንጋዩን እየወረወርን የፈነከትናቸው ስንቶች ይሆኑ ?

      ድል የማድረጊያ አንዱ መንገድ ብርቱዎቹን መደገፍ ነው፤ ክንዳቸው፣ ድምጻቸው፣ ሥራቸው፣ ጥረታቸው፣ ሐሳባቸው፣ ራዕያቸው ከፍ ሲል ድል እንዲያደርጉ መደገፍ ነው፡፡ መጥፎ ሠሪዎችን የምንቃወመውን ያህል መልካም ሠሪዎችን የማንደግፍ ከሆነ ውጤት አናመጣም፡፡

የሙሴም ታላቅነት ምን መሪ ቢሆን፣ እጆቹ ታላቅ ሥራ የሚሠሩና ድል አድራጊ ቢሆንም ሊደክም፣ ሊሸነፍ፣ ሊያቅተውና ሊዝል እንደሚችል አመነ፡፡ ያለ ሌሎች ድጋፍ ብቻውን ለውጥ እንደማያመጣ ተቀበለ፡፡ ታላቅነት ማለት የታናናሾችን አስተዋጽዖ መናቅ አይደለም፡፡ ሁሉን ብቻዬን አደርገዋለሁ አላለም፡፡ አሮንና ሖር እንደሚያስፈልጉት ተቀበለ፡፡ ጎበዝ ሰው እንዲህ ነው፡፡ ሁሉንም ለብቻዬ እችለዋለሁ አይልም፡፡ የአንድ ሰው ውጤታማነት የብዙ ሰዎች አስተዋጽዖ ውጤት ነውና፡፡ ድል የሙሴም፣ የአሮንና የሖርም የየብቻ ውጤት አይደለም፡፡ ድል የሙሴ፣ የአሮንና የሖር የኅብረት ውጤት ነው፡፡ ስለዚህ በፍቅር በህብረት ለድል እጅ ለእጅ እንያያዝ አሜን፡፡

በዚህ እና በሌሎችም ጽሁፎች ተባርከው ከሆነ ገጹን ላይክ ቢያደርጉ አስተያየቶትንም ቢያሰፍሩልኝ ደስተኛ ነኝ አመሰግናለሁ።

ካሱ ቦስተን

እባክዎን ካነበቡ በኋላ ላይክ የሚለውን ይጫኑ እንዲሁም መልእክቱን ለሌሎች ያካፍሉ አመሰግናለሁ

የእግዚአብሄርን ቤት ጓዳዎች እናፅዳ

በነህምያ ዘመን እንዲህ ሆነ፡፡ ነህምያ የኢየሩሳሌምን መፍረስና የበሮችዋን መቃጠል በሰማ ጊዜ እጅግ አዘነ አለቀሰም፡፡ ከዚያም ከንጉሡ ፈቃድ አግኝቶ ኢየሩሳሌምን ሊሰራ በመጣ ጊዜ ሶስት ጠላቶች ተነሱበት፡፡ “ሐሮናዊውም ሰንበላጥ ባሪያውም አሞናዊው ጦቢያ ዓረባዊውም ጌሳም በሰሙ ጊዜ በንቀት ሳቁብን፡፡ ቀላል አድርገውንም ይህ የምታደርጉት ነገር ምንድን ነው? በውኑ በንጉሡ ላይ ትሸፍቱ ዘንድ ትወዳላችሁን? አሉን፡፡” ይላል (ነህ.2፥19) ከዚህም ሌላ በብዙ ማስፈራራትና ዛቻ፣ በደብዳቤም በሰውም ኢየሩሳሌም እንዳትሰራ የነህምያን ልብ ለመስበር ሞክረዋል፡፡ ነህምያ ግን የአምላኩ እጅ ከርሱ ጋር ነበረችና ሥራውን ጨረሰ

    ይህ ሁሉ ከሆነ በኋላ ግን የኢየሩሳሌምን መሰራት ሲቃወም የነበረው ጦቢያ መኖሪያ ፍለጋ ወደ መቅደሱ አዘገመ። ኤልያሴብ ከሚባለው ካህን ጋር በመወዳጀትም በእግዚአብሔር ቤት ጓዳ ለመቀመጥ ቻለ፡፡ ነህምያ ስለዚህ ነገር ሲናገር እንዲህ ይላል“ከዚህም አስቀድሞ በአምላካችን ቤት ጓዳዎች ላይ ተሹሞ የነበረው ካህኑ ኤልያሴብ ከጦቢያ ጋር ተወዳጅቶ ለሌዋውያንና ለመዘምራን ….. እንደ ህጉ የተሰጣቸውን ለካህናቱም የሆነውን የማንሳት ቁርባን አስቀድሞ ያስቀመጡበትን  ታላቁን ጓዳ አዘጋጅቶለት ነበር፡፡» (ነህ.13፥4-6) ይህ መንፈሳውያን ለሆኑ ሁሉ ታላቅ መልእክት አለው፡- የኢየሩሳሌምን መታነፅና መታደስ በፅኑ ሲቃወም የነበረው ተቃዋሚ ጠላት ጦቢያ ከእግዚአብሔር ቤት ውስጥ  ታላቁን ጓዳ ሲያገኝና በዚያ ሲቀመጥ ለነህምያና ዛሬም የነህምያ መንፈስ ለሆነላቸው እንዴት የሚያሳዝንና የሚያበሳጭ ነው ! ያውም የተሰጠው ታላቁ ጓዳ እንደህጉ ለሌዋውያን ለመዘምራን ለበረኞች ለካህናት በአጠቃላይ ለመቅደሱና ለታላቁ ንጉሥ ለእግዚአብሔር አገልጋዮች የተዘጋጀው መብል የሚቀመጥበት የከበረው ቦታ ነበር፡፡ መብል በሚቀመጥበት ቦታ  ውስጥ የእግዚአብሔር ህዝብ ጠላት ተቀምጦ ነበር፡፡ (ሚል.3፥10)

   ዛሬም በዚህ ቃል ራሳችሁንና መቅደሳችሁን ማለትም እግዚአብሄርን ማምለኪያና ህብረት ማድረጊያ ስፍራዎቻችሁን እንዲሁም መንፈሳዊ ጓዳችሁን ፈትሹ፡፡ ከካህኑ ወይም ከሐሰተኛ አገልጋዮች ጋር ተወዳጅቶ የእውነት ዓምድና መሰረት በሆነው በእግዚአብሔር ቤት ጓዳ ውስጥ የተቀመጠውን የዘመኑን ጦቢያ ሃሰተኛና አስመሳዩን ንቁበት፡፡ ይህም የዘረኝነት የግለኝነት (ቤተክርስቲያንን እንደግል ንብረት ማየት) የመጣላት የመለያየትና የመከፋፈል ምክንያት የሆነው አሮጌው ሰው ነው ፡  

     በእግዚአብሔር ቤት ውስጥ በተለይ አሁንም ጦቢያ “አሮጌው ሰው” ገዝፎ የሚታየው በታላቁ የአገልጋዮች የመዘምራን የሌዋውያን ጓዳ ነውና ነህምያዎች ሆይ ይህንን ጓዳ ለማፅዳትና ለእግዚአብሔር ለመቀደስ “ለመለየት” ትጉ፡፡ 

   ነህምያ ያደረገውን ተመልከቱ “ኤልያሴብም በእግዚአብሔር ቤት አደባባይ ለጦቢያ ጓዳውን በማዘጋጀት ያደረገውን ክፉ ነገር አስተዋልሁ፡፡ እጅግም አስከፋኝ፡፡ የጦቢያንም የቤቱን እቃ ሁሉ ከጓዳ ወደ ውጭ ጣልሁ፡፡ ጓዳዎቹንም እንዲያነፁ አዘዝሁ፡፡ የእግዚአብሔርንም ቤት እቃዎች፣ የእህሉንም ቁርባን፣ እጣኑንም መልሼ በዚያ አገባሁ” (ነህ.13፥7-9) ይህ መልእክት ለኛም በዚህ ዘመን ላለን የወንጌል መልእክተኞች የተሰጠ የአደራ መልእክት ነው፡፡ የእግዚአብሔርን ቤት ጓዳዎች እናፀዳ ዘንድ ይገባል፡፡ (ሮሜ.12፥1) ከጦቢያ፣ ከአሮጌው ሰው፣ ከስጋዊ ማንነት የፀዳ፣ የእውነት ዓምድና መሰረት የሆነውንም እውነተኛ የእግዚአብሔር መቅደስ ማግኘት ያስፈልገናል፡፡ ጦቢያ በተቀመጠበት ጓዳ የጠራና የሰባ የመንፈስ መብል የለምና፡፡ 

    መንፈሳዊ ቤት ሆኖ ለመሰራት ጓዳን ማጽዳት አስፈላጊ መሆኑን ልንገነዘብ ያስፈልጋል ፡፡ ጓዳን ማጽዳት ስል ያለ እግዚአብሄር ጸጋ የሚያገለግሉ የሚያስተምሩ የሚሰብኩ የሚዘምሩ እረኛ ነብያት ሃዋርያት የሆኑ እነዚህን ለይተን ማጽዳትና ጸጋው ያላቸውን መተካት ያስፈልጋል ባይ ነኝ ቤቱ አዲስ ሲሆን ልንረሳው የማይገባን ነገር ከአሮጌ ቤት አሮጌ እቃ ለቤቱ እንደማይመጥነው ለአዲሱ መንፈሳዊ ቤትም በአዲስ ቅባት የተቀቡ ለቤቱ የሚመጥኑ የመገልገያ እቃዎች ያስፈልጋሉና ይህንን ነህምያዎች ነቅተው እንዲለዩት ቤቱን እንዲያሳምሩት ያስፈልጋል

   ሌላው ደግሞ ዛሬ ጦቢያ ሆኖ በቤተክርስቲያን የተቀመጠ አላፈናፍን ያለና የእግዚአብሄርን መንፈስ ያዳፈነ የሰው ስርዐት ደንብና ህግ ይሆን ?? የእግዚአብሄር ህዝብ ሆይ ልንነቃ ይገባናል፡፡ ተባረኩልኝ፡፡

እባክዎን አንብበው ሲጨርሱ ላይክ የሚለውን ቢጫኑት ወደፊት የሚወጡ ጽሁፎችን በቀላሉ ማግኝት ይችላሉ በማንበብ ስለሚተባበሩኝም አመሰግንዎታለሁ

ካሱ ቦስተን

እባክዎን ካነበቡ በኋላ ላይክ የሚለውን ይጫኑ እንዲሁም መልእክቱን ለሌሎች ያካፍሉ አመሰግናለሁ

  ቅዱሳን ሁኑ !

 ዳሩ ግን፦ እኔ ቅዱስ ነኝና ቅዱሳን ሁኑ ተብሎ ስለ ተጻፈ የጠራችሁ ቅዱስ እንደ ሆነ እናንተ ደግሞ በኑሮአችሁ ሁሉ ቅዱሳን ሁኑ። 

(1ኛ የጴጥሮስ መልእክት1:15-16)  

​(ትንቢተ ሕዝቅኤል 36:20-23)

ወደ መጡባቸውም ወደ አሕዛብ በመጡ ጊዜ፥ ሰዎች እነርሱን፦ ከምድሩ የወጡ የእግዚአብሔር ሕዝብ እነዚህ ናቸው ሲሉአቸው ቅዱስ ስሜን አረከሱ። እኔ ግን የእስራኤል ቤት በመጡባቸው በአሕዛብ መካከል ስላረከሱት ስለ ቅዱስ ስሜ ስል ራራሁላቸው። ስለዚህ ለእስራኤል ቤት እንዲህ በል፦ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ የእስራኤል ቤት ሆይ፥ በመጣችሁባቸው በአሕዛብ መካከል ስላረከሳችሁት ስለ ቅዱስ ስሜ ነው እንጂ ስለ እናንተ የምሠራ አይደለሁም። በአሕዛብም ዘንድ የረከሰውን፥ በመካከላቸው ያረከሳችሁትን ስሜን እቀድሰዋለሁ፤ በዓይናቸውም ዘንድ በተቀደስሁባችሁ ጊዜ እኔ እግዚአብሔር እንደ ሆንሁ አሕዛብ ያውቃሉ፥ ይላል ጌታ እግዚአብሔር፡፡

     እግዚአብሄር እኔ በአህዛብ ፊት እናንተን ከነርሱ ውጡና የተለያችሁ ሁኑ እርኩሱንም ነገር አትንኩ ብያችሁ ነበር ነገር ግን እናንተ በመሃከላቸው ሆናችሁ ቅዱሱን ስሜን አረከሳችሁት: ስለዚህ እኔ እንደሎጥ እራራላችሁና እጃችሁን ይዤ አወጣችኋለሁ ለራሴ ለቅዱሱ ስሜ ስል እቀድሳችኋለሁ: ያኔ እናንተን ስቀድስ መልካም አድርጌ ስሠራችሁና በናንተ ውስጥ ስኖር አህዛብ እኔ እግዚአብሄር እንደሆንኩ ያውቃሉ እኔ እራሴ ስሜን አስከብራለሁ እናንተን እቀድሳለሁ እንደገናም በእናንተ እቀደሳለሁ ይላል ይህን የማደርገው ግን እናንተ ስለሰራችሁት ስለመልካም ስራችሁ ሳይሆን ስለራሴ ቅዱስ ስለሆነው ስሜ ነው ይላል ምክኒያቱም እኔ ቅዱስ ነኝና እናንተም ቅዱሳን እንድትሆኑ ስለምፈልግና እኔንም ማየት የምትችሉት በቅድስና ስትኖሩ ስለሆነ ነው፡፡

   እንግዲህ መንፈሳዊ ቤት ሆናችሁ እንድትሰሩና እኔ እንድኖርባችሁ ይህን ከዚህ የሚቀጥለውን በመካከላችሁ አደርጋለሁ ይላል እግዚአብሄር፡፡

     ከአሕዛብም መካከል አወጣችኋለሁ፥ ከየአገሩም ሁሉ እሰበስባችኋለሁ፥ ወደ ገዛ ምድራችሁም አመጣችኋለሁ። ጥሩ ውኃንም እረጭባችኋለሁ፥ እናንተም ትጠራላችሁ፥ ከርኵሰታችሁም ሁሉ ከጣዖቶቻችሁም ሁሉ አጠራችኋለሁ። አዲስም ልብ እሰጣችኋለሁ፥ አዲስም መንፈስ በውስጣችሁ አኖራለሁ፤ የድንጋዩንም ልብ ከሥጋችሁ አወጣለሁ፥ የሥጋንም ልብ እሰጣችኋለሁ። መንፈሴንም በውስጣችሁ አኖራለሁ፥ በትእዛዜም አስሄዳችኋለሁ፥ ፍርዴንም ትጠብቃላችሁ ታደርጉትማላችሁ። ለአባቶቻችሁም በሰጠኋት ምድር ትኖራላችሁ፤ ሕዝብም ትሆኑኛላችሁ እኔም አምላክ እሆናችኋለሁ። (ትንቢተ ሕዝቅኤል 36:24-28) አሜን አሜን አሜን!!!

እባክዎን አንብበው ሲጨርሱ ላይክ የሚለውን ቢጫኑት ወደፊት የሚወጡ ጽሁፎችን በቀላሉ ማግኝት ይችላሉ በማንበብ ስለሚተባበሩኝም አመሰግንዎታለሁ

ካሱ ቦስተን

እባክዎን ካነበቡ በኋላ ላይክ የሚለውን ይጫኑ እንዲሁም መልእክቱን ለሌሎች ያካፍሉ አመሰግናለሁ