እውነተኛ ደቀ መዝሙር

 ክፍል 3

በክፍል 2 ጽሁፌ ላይ በዛሬይቱ ቤተ ክርስቲያን መለኪያ እንኳንስ ወደ ኋላ ተመለሱ ሊባሉ ይቅርና «መሪና አገልጋይ ተብለው ሊሾሙ የሚችሉ ሰዎችን ጌታ ኢየሱስ ግን «ለደቀ መዝሙርነት ብቁ አይደላችሁም» ብሎ የርሱን የደቀ መዝሙርነት መለኪያ ያለፉትናና ወደኋላ የተመለሱትን ጥቂት ሰዎች እንመለከታለን ብዬ ቀጠሮ በሰጠኋችሁ መሰረት እነዚህን ሰዎች ማየት እንጀምራለን ለዛሬ አንድ ባለጸጋ ሰው እንመልከት፦ 

ባለጸጋው።

“እርሱም በመንገድ ሲወጣ አንድ ሰው ወደ እርሱ ሮጦ ተንበረከከለትና። ቸር መምህር ሆይ፥ የዘላለም ሕይወትን እወርስ ዘንድ ምን ላድርግ? ብሎ ጠየቀው። ትእዛዛትን ታውቃለህ፤ አታመንዝር፥ አትግደል፥ አትስረቅ፥ በሐሰት አትመስክር፥ አታታልል፥ አባትህንና እናትህን አክብር አለው። ኢየሱስም፦ ስለ ምን ቸር ትለኛለህ? ከአንዱ ከእግዚአብሔር በቀር ቸር ማንም የለም። እርሱም መልሶ፦ መምህር ሆይ፥ ይህን ሁሉ ከሕፃንነቴ ጀምሬ ጠብቄአለሁ አለው።» ይህ ሰው በዚህ ዘመን ካሉት አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ ውስጥ በ99.9 ከመቶ ተቀባይነት የሚያገኝና ወደ መሪነት ሊደርስ የሚችል ሰው ለመሆኑ ከራሳችን ሌላ ምስክርን አንሻ። 

በመጀመሪያ፦ ሲመጣ ሮጦ ነው የመጣው ይህም ጌታን ለመከተል ያለውን ጉጉት ያሳያል። 

ሁለተኛ፦ «ቸር መምህር ሆይ» ብሎ ነው የጠራው (ኢየሱስ ጌታ ነው ማለቱ ነው)። 

ሶስተኛ፦ እንዲሁ ዝም ብሎ ሳይሆን የቀረበው እየሰገደ ተንበርክኮ ነው። ይህም ለጌታ ክብርን መስጠቱ ነው። 

    ይህ ፍጹም የሆነ መታዘዝና መገዛትን የሚያሳይ የሚመስል አቀራረብ ነው። እንዲህ እያደረገ ወደኛ ወይም ወደ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያናችን የሚመጣን ሰው ደፍሮ ሌላ ጥያቄ የሚጠይቅ ሰው ይኖር ይሆን? በተለይ ይህ ድርጊቱ በመሪዎችም ላይ ያነጣጠረ ከሆነማ ያለምንም «ይለፍ» ነው ሰተት ብሎ የሚገባው። ኢየሱስ ግን ለርሱ እየተንበረከከና «ቸር መምህር ሆይ» እያለ ወደርሱ የመጣውን ሰው ወደ አባቱና ወደ ቃሉ ነው ያስተላለፈው። ለርሱ ባሳየው የግብዝነት አመጣጥ ሳይሆን በቃሉ መዘነው። ኢየሱስ ሰዎችን የሚመዝነው ሰዎች ለእግዚአብሔር ቃል ባላቸው መታዘዝ ብቻ ነውና። እርሱን ጌታና መምህር እያሉ የአባቱን ፈቃድ የማያደርጉትን አይሻም “በሰማያት ያለውን የአባቴን ፈቃድ የሚያደርግ እንጂ፥ ጌታ ሆይ፥ ጌታ ሆይ፥ የሚለኝ ሁሉ መንግሥተ ሰማያት የሚገባ አይደለም።” በማለት አስረግጦ ተናግሮአል። የአባቱን ፈቃድ ሊፈጽም እንጂ ለራሱ ክብርን ሊሻ አልመጣምና። ስለዚህ ቸርና ደግ መምህር እንደሆነ እየተናገሩ የሚመጡትን ሁሉ ወደ አባቱ ፈቃድ ይመራቸዋል። (ማቴ.7፡21 ዮሐ.3:1-3)

ይህ ሰው ለደቀ መዝሙርነት ባልተዘጋጀ ልብ ቸር መምህር ሆይ እያለ ሲቀርብም ያገኘው መልስ እንዲህ የሚል ነበር “ኢየሱስም፦ ስለ ምን ቸር ትለኛለህ? ከአንዱ ከእግዚአብሔር በቀር ቸር ማንም የለም። ትእዛዛትን ታውቃለህ፤ አታመንዝር፥ አትግደል፥ አትስረቅ፥ በሐሰት አትመስክር፥ አታታልል፥ አባትህንና እናትህን አክብር አለው። እርሱም መልሶ፦ መምህር ሆይ፥ ይህን ሁሉ ከሕፃንነቴ ጀምሬ ጠብቄአለሁ አለው።” የሚገርም ነው። ይህን ሁሉ ትእዛዝ ከህጻንነቱ ጀምሮ የፈጸመ ሰው ከሆነማ ሌላ ምን ይጠየቃል? መምህሩ ግን ወደደውና የመጨረሻውን ክቡር ጥሪ ጠራው “። ኢየሱስም ወደ እርሱ ተመልክቶ ወደደውና። አንድ ነገር ጐደለህ፤ ሂድ፥ ያለህን ሁሉ ሽጠህ ለድሆች ስጥ፥ በሰማይም መዝገብ ታገኛለህ፥ መስቀሉንም ተሸክመህ ና፥ ተከተለኝ አለው።” ልብ በሉ የኢየሱስ ደቀ መዝሙር ለመሆን አንድ ነገር ብቻ ነው የቀረው እንግዲህ ያንን ሁሉ ትእዛዝ ከህጻንነቱ ጀምሮ የፈጸመ ሰው አንድ ነገር ይከብደዋል ትላላችሁ? ግን ከበደው። “ነገር ግን ስለዚህ ነገር ፊቱ ጠቈረ፥ ብዙ ንብረት ነበረውና እያዘነም ሄደ።” ጌታ ቸር መምህር እንደሆነ፣ የዘላለም ህይወት በርሱ እንደሚገኝ አውቆ እንዴት ተመልሶ ይሄዳል? ያለው ኃብትና ብልጽግናስ እንዴት ከኢየሱስ በለጠበት? ይህንን ስናነብ ለመመለሱ ምክንያት ሆኖ የተቀመጠው ብዙ ኃብት ነው ግን የማን ኃብት? የሚለውን መጠየቅ አለብን። አለዚያ ሃብቱን ብቻ እናይና በሃብቱ ውስጥ የተደበቀውን እኔ (እኔነት) እንረሳለን ሃብቱን ከኢየሱስ አስበልጦ ያሳየው ያ በመስቀል ካልሆነ የማይሞተው ማንነቱ ነው። እኔነታችን ካልሞተና መስቀላችንን ካልተሸከምን ኢየሱስን መከተል የማንችለው ለዚህ ነው። አሮጌው ሰው አዳም መስቀልን እንጂ ኢየሱስን አይጠላም መስቀል የሌለው ኢየሱስ ቢያገኝ ኖሮ በጣም ደስ ይለዋል። እርሱ ራስና አዛዥ እንደሆነ ኢየሱስን መከተል ቢችል ከእኔነቱ በስተቀር ሁሉን ለጌታ ሰጥቶ መንፈሳዊ መባልን ይወዳል። አዳም የሚጠላው እርሱን ገድሎ እልቅናውን የሚወስድበትን ኢየሱስ ብቻ ነው። እውነተኛው ኢየሱስ ደግሞ ከመስቀል ተለይቶ አይገኝም። ስለዚህ ኢየሱሰ ወደ እኛ ህይወት ሲመጣ የመጀመሪያ ስራው በመስቀሉ ሥራ አሮጌነታችንን ማስወገድ ነው። 

    የርሱ ቅርንጫፎች የሆኑት ሁሉ ግን በርሱ መወገድ ብቻ ይወገዳሉ። የዛፍ ግንድ ቅርንጫፎቹን ቅጠሉንና ፍሬውን ያመነጨና የተሸከመ የዛፉ ዋነኛ ክፍል ሲሆን ቅርንጫፎቹ ፍሬዎቹና ቅጠሎቹ የግንዱ ወይም የዛፉ ናቸው። እኔነት ደግሞ «የኛ» የምንላቸውን ነገሮች ሁሉ የሚቆጣጠር የሰው ግንዱ ነው። ስለዚህ ሰው ስለማንነቱ ሲጠየቅ «እኔ» ይልና ስላለው ነገር ሁሉ ሲጠየቅ «የኔ» ይላል። እንግዲህ «የኛ» የምንላቸው ነገሮች ሁሉ የተንጠለጠሉት በ«እኔ» ላይ ነው። አንድ ሰው ከላይ እንዳየነው ባለጸጋ እኔነቱን ሳይለቅ በእኔነቱ እንዳለ ሆኖ ብዙ ነገርን ሊያደርግ እግዚአብሔርንም ሊያገለግል ይችላል። 

    ሰው እኔነቱን ሳይለቅ የሚያገኛቸው ነገሮች በሙሉ “የእኔ” ብሎ እንደሚጠራቸው አይተናል። በመሆኑም ሰው እኔነቱ ሳይሞት ኢየሱስን እከተላለሁ ቢል፣ ቸር መምህር ሆይ ብሎ ቢጠራው ፣ሃይማኖተኛ ቢሆን፣ ትእዛዛቱን ለመፈጸም ቢተጋ ይህ ሁሉ ስለ «እኔ» ወይም ለ«እኔ» ነው። ያለውን ሃብት ሁሉ «የእኔ» እንደሚል፡- ሃይማኖቱንም፣ ኢየሱስንም የኔ ብሎ ይቆጥራል፣ ያስባል። ለምን ትእዛዛቱን ይፈጽማል? ራሱን እኔነቱን ስለሚወድ ሲኦል እንዳይገባበት፣ በምድር በብዙ ጥረት ፍላጎቱን አሟልቶለት ያኖረው እኔነቱ ሲሞትም የሰማዩን እንዳያጣ ያስብለታል። በላይ በሰማይ በወርቅ ቤት እንዲኖርና በምድር ሙሉ በሙሉ ያልረካው ማንነቱ በላይ እንዲረካለት መንፈሳዊ ለመሆን ይተጋል። እውነተኛው ክርስትና ግን ኢየሱስን «ለእኔ» መቀበል ሳይሆን «እኔን» ለኢየሱስ ማስለቀቅና «እኔን» በመስቀሉ ገድሎ «በእኔ» ምትክ ክርስቶስን ማኖር ነው። ይህ ገብቶት ክርስቶስን የተቀበለው ሐዋርያ እንዲህ ያውጃል፦ “ከክርስቶስ ጋር ተሰቅዬአለሁ፤ እኔም አሁን ሕያው ሆኜ አልኖርም ክርስቶስ ግን በእኔ ይኖራል፤ አሁንም በሥጋ የምኖርበት ኑሮ በወደደኝና ስለ እኔ ራሱን በሰጠው በእግዚአብሔር ልጅ ላይ ባለ እምነት የምኖረው ነው።” (ገላ.2:20)

   ከላይ ያየነውን ባለጸጋ ሰው በዚህ ሚዛን ስናየው ዘመኑን ሁሉ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ሲፈጽም የኖረው ወደ ዘለዓለም ህይወት ለመግባት ለመሆኑ ከጥያቄው እንረዳለን። ችግሩ ያለው የዘላለምን ህይወት መፈለጉ አይደለም። ያንንማ ሁላችንም መፈለግ አለብን። ነገር ግን ይህንን ህይወት ለመውረስ የምንሄድበት መንገድና ይህን ህይወት ለማን እንደፈለግነው አለማወቃችን ላይ ነው። በዚህ ስፍራ ሰውየው ፈልጎ የመጣው የዘላለምን ህይወት ነው። ጌታ ኢየሱስም ለዚህ ሰው የዘላለምን ህይወት የሚያገኝበትን መንገድ ነው የነገረው። እንግዲህ ልዩነቱ ምንድን ነው? ልዩነቱማ ሰውየው የዘላለምን ህይወት የፈለገው «የእኔ» ከሚላቸው እንደ አንዱ የሚቆጥረው፣ በእኔነቱ ስር የሚገዛ፣ «አለኝ» የሚለው የዘላለም ህይወት እንዲኖረው ሲሆን እውነተኛውና ጌታ የሰጠው የዘላለም ህይወት ግን እኔነቱን የሚያጠፋና ከዚያ በፊት እኔነቱ የሚቆጣጠራቸውን ነገሮች ሁሉ አጥፍቶ ክርስቶስን ህይወቱ የሚያደርግ የዘላለም ህይወት ነው። 

የዘላለም ህይወት አሁን እኔነቱ ከያዘው ሃብት ጋር ጨምሮ «የኔ» የሚለው ህይወት ሳይሆን የርሱን እኔነት አጥፍቶ በርሱ የሚኖር ህይወት ነው። ስለዚህ ያለህን ሁሉ ሽጥና መስቀልህን ተሸክመህ ተከተለኝ ተባለ። ባለው ላይ ሊጨምር መጥቶ ሁሉን እንዲያጣ ተነገረው። በዚህም የምንማረው የዘላለም ህይወት ማለት እኔነታችን «አለኝ» ከሚላቸው ነገሮች ጋር ቆጥረን የእኔነታችን ንብረት የምናደርገው ሳይሆን እኔነታችንና «የኔ» የምንለውን ሁሉ ትተን የምናገኘው ክርስቶስ ነው። “ነፍሱን ሊያድን የሚወድ ሁሉ ያጠፋታል፤ ስለ እኔ ግን ነፍሱን የሚያጠፋ ሁሉ ያገኛታል።” (ማቴ.16፡25) በዚህ ቃል መሰረት ይህ ሰው የተጠየቀው ነፍሱን ያገኛት ዘንድ እንዲያጠፋት ነው። እርሱ ግን ሊያድናት ስለወደደ አጠፋት። እንግዲህ ቃሉን በሚገባ ስንረዳው ሰውየውን ወደኋላ የመለሰው ኃብቱ ሳይሆን እኔነቱ ነው። ኃብቱ የእኔቱ ስለሆነ እኔነቱና ሃብቱ ደግሞ መስቀል ካልተሸከመ በቀር የማይለያዩና የተጋቡ ስለሆኑ፡ መስቀል መሸከምን የጠላው እኔነቱ በኃብቱ አመካኝቶ መለሰው። እኔነቱ መስቀሉን ቢሸከም ኖሮ ግን ኃብቱ በርሱ ላይ አቅምን ያጣል። እኔነት የለውምና ምኑን ይዞ ይጎትተዋል? እንግዲህ ይህ ሰው እኔነቱን ሳይክድና መስቀሉን ሳይሸከም ይህን ያህል አስገራሚ መንፈሳዊ ጉዞ መጓዙ አዳም ለምድር ብቻ ሳይሆን የዘላለምን ህይወትም በወዙ ለማግኘት እስከ መስቀል ጥግ ድረስ መሄዱ እንደማይቀር እንድንገነዘብ ይረዳናል። ህይወትን የምናገኝበትና የኢየሱስ ደቀ መዝሙር የምንሆንበት መንገድ መስቀልን ተሸክሞ ኢየሱስን መከተል ብቻ መሆኑ ግን ሌሎች ትጋቶቻችን ሁሉ ከመስቀሉ ወዲህ ያሉ ከንቱ የአዳም ጥረት አድርጎአቸዋል። ይገርማል በዚህ ሰው ልብና አስተሳሰብ ሆነን ትእዛዛቱን ሁሉ ፈጸምን ብንል እንኳ መስቀሉን ተሸክመን ኢየሱስን ካልተከተልን እንደዚህ ሰው እያዘንን ከመመለስ በቀር ሌላ ምርጫ የለንም። ጌታ ከዚህ ያነሰ መለኪያ የለውምና። እርሱስ ተፈጸመ ያለው በመስቀል ላይ አይደል? እኛ መስቀሉን ሳንሸከምና አሮጌ ማንነታችን ሞቶ ክርስቶስ በኛ ሳይኖር ከመስቀሉ ማዶ ሆነን ተፈጸመ (ሁሉን ፈጽሜአለሁ) ማለታችን ለምን ይሆን? ዛሬ ለኛ መለኪያው የተቀነሰ ይመስል ከዚህ ሰው እንኳ ያነሰ ምልልስ እየተመላለስን የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ለመባል መድፈራችን ግን የመጽሐፍ ቅዱሱን ኢየሱስ እጅግ አሳዝኖታል። ቢወደንም ከርሱ ጋር የምንሆንበትን መንገድ አበክሮ ከመናገር አላቋረጠም። እርሱም “መስቀላችንን ተሸክመን እንድንከተለው መጣራቱ ነው። ቀጣዩን ደግሞ በክፍል 4 እናነባለን ይጠብቁን።

ካሱ ቦስተን

እባክዎን ካነበቡ በኋላ ላይክ የሚለውን ይጫኑ እንዲሁም መልእክቱን ለሌሎች ያካፍሉ አመሰግናለሁ

እውነተኛ ደቀ መዝሙር

ክፍል 2

ደቀመዝሙር ማለት ወደኋላ የማያይ ጌታውን ብቻ እየተከተለ ወደፊት የሚሄድ ነው። “ማንም ዕርፍ በእጁ ይዞ ወደ ኋላ የሚመለከት ለእግዚአብሔር መንግሥት የተገባ አይደለም” ተብሎ ተፅፎአልና። ጌታ የሎጥን ሚስት አስቧት ያለን ለምን ይሆን? ከወጡ፣ ካመለጡ ፣ከዳኑ በኋል መጥፋት ስላለ አይደለምን? የሎጥ ሚስት ወደኋላ አልሄደችም ግን በልቧ ወደ ኋላ ሄደች። ጌታ አካላችን ያለበትን ሳይሆን ልባችን ላበትን ያያል፡ ደቀ መዝሙር የሚያደርገን፡- የልብ እምነት፣ የልብ መገረዝ፣ የልብ ውሳኔና ጭካኔ እንጂ በውጭ የምናሳየው ግብዝነት አይደለም። ጌታን ስንከጽሁፌ ላይ እንደገለጽኩት.  በማለት ሃሳቤን አስፍሬ ነበር እንዴት ነው የምንቀንሰው የሚለውን እናያለን ጽሁፌ ላይ እንደገለጽኩት.  በማለት ሃሳቤን አስፍሬ ነበር እንዴት ነው የምንቀንሰው የሚለውን እናያለን ተል በእግራችን ሳይሆን በልባችን እየተከተልነው መሆኑን ይመዝነናል።

በክፍል 1. ጽሁፌ ላይ እንደገለጽኩት ደቀመዝሙር ያልሆነውንና የኢየሱስ ወንጌል የማያረካውን ህዝብ ከአዳራሾቻችን መቀነስ አለብን በማለት ሃሳቤን አስፍሬ ነበር እንዴት ነው የምንቀንሰው የሚለውን እናያለን፦

ቤተ ክርስቲያን ህዝቡን በእውነተኛና ማመቻመች በሌለበት ንጹህ ቃል በመመገብ ምእመኑ እራሱን ክዶ መስቀሉን እየተሸከመ እንዲጓዝ የሚያደርግ ምግብ በመመገብ ነው፥ አለበለዚያ በየጊዜው ኮንፍራንስ እያዘጋጀንና የተመኙትን የሚሰብኩላቸውንና የሚተነብዩላቸውን እየጋበዝን ከቀጠልን ግን ለሚጠፋ መብል ኢየሱስን የሚከተል ብዙ ህዝብ እንደያዝን እንሰነብታለን። 

ብዙ አብያተ ክርስቲያናት በኢየሱስ ወንጌል መለኪያ ተለክተው ያላለፉትንና ወደ ኋላ የተመለሱትን ሰዎች ሰብስበው ትልቅ ቤተ ክርስቲያን ተብለው መጠራታቸው ከኢየሱስ የተለየ ሌላ ወንጌል እየሰበኩ መሆናቸውን አጋልጦባቸዋል። ለመሆኑ እነዚያን በኢየሱስ መለኪያ ያላለፉትን ዛሬ ያሉት አብያተ ክርስቲያናት የት አግኝተዋቸው ነው ደቀመዝሙር ያደረጓቸው? የሚል ካለ እነዚያን ኢየሱስ የመለሳቸውን ሰዎች አይነት ልብና አመለካከት ይዘው የመጡትን እነዚያን መቀበላቸው መሆኑ ሊገባን ይገባል። ይህን ስንል ብዙ ወንድሞችና እህቶች ያሏቸው አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ ሐሰትን ሰብከዋል ማለት ሳይሆን በዚህ መለኪያ ያላለፉ ብዙ ሰዎችን መሰብሰባቸውን መግለጻችን ነው። ምናልባት አንዳንዶቻችን ኢየሱስ ብዙ ሰዎችን ወደርሱ እንዲመጡ ይጠራ ነበር እንዲያውም “እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ፥ ወደ እኔ ኑ፥ እኔም አሳርፋችኋለሁ።” አላለም ወይ? እንል ይሆናል አዎ ብሎአል። የመጣውም ደካሞችን ኃጢአተኞችን ሊጠራና ሊያድን ነው። ይሁን እንጂ እነዚህ የተጠሩት ደካሞች ለመዳን በዚህ መለኪያ ማለፍ አለባቸው። ኢየሱስ እነዚህን ሁለቱን መልእክቶች መሳ ለመሳ አንዱን ከአንዱ ሳይለይ ነው ያወጀው። ሰው ሁሉ በርሱ እንዲያምንና እንዲከተለው እየተጣራ መለኪያን ግን እንደየሰው ፍላጎትና ቁጥር አልቀነሰም። ለተጠሩት ሁሉ መለኪያው አንድ ነው። አንድም ቀን ኢየሱስ ይህንን መለኪያ ዝቅ አላደረገም። ምክንያቱም ወደ ህይወት የሚወስደው መንገድ ጠባብ ነው። ህይወትን ሊያገኝ የወደደ ሁሉ በዚያ መንገድ ማለፍ አለበትና። ለዚህም ነው በዛሬይቱ ቤተ ክርስቲያን መለኪያ እንኳንስ ወደ ኋላ ተመለሱ ሊባሉ ይቅርና «መሪና አገልጋይ ተብለው ሊሾሙ የሚችሉ ሰዎችን ጌታ ኢየሱስ ግን «ለደቀ መዝሙርነት ብቁ አይደላችሁም» ብሎ የመለሰው። እስኪ ለምሳሌ የርሱን የደቀመዝሙርነት መለኪያ ያለፉትናና ወደኋላ የተመለሱትን ጥቂት ሰዎች እንመለከታለን፦  በክፍል 3 ይቀጥላል …

ካሱ ቦስተን

እባክዎን ካነበቡ በኋላ ላይክ የሚለውን ይጫኑ እንዲሁም መልእክቱን ለሌሎች ያካፍሉ አመሰግናለሁ

እውነተኛ ደቀ መዝሙር !

ክፍል 1 

እውነተኛ ደቀ መዛሙርት ልባቸውን በዓለም አስቀምጠው ነፍሳቸውን እየተንከባከቡ ባላቸው ላይ እንዲጨመርላቸው ጌታን ለመጠየቅ ወደ የጸሎት ቤቱ የሚጎርፉት ሳይሆኑ ሁሉን ትተው የተከተሉት ናቸው። «በዚያን ጊዜ ጴጥሮስ መልሶ፦ እነሆ፥ እኛ ሁሉን ትተን ተከተልንህ፤ እንኪያስ ምን እናገኝ ይሆን? አለው።» ጌታ ግማሽ ትቶ የተከተለው ደቀ መዝሙር አልነበረውም። ዛሬ ዛሬ ይህ ሁሉን ትቶ ኢየሱስን የመከተልና የርሱ ደቀመዝሙር የመሆን ጥሪ የተለወጠ ወይም የተረሳ ይመስላል። አንዳንዶቻችንም ለመጀመሪያዎቹ ደቀ መዛሙርት ብቻ የተቀመጠ መርህ ይመስለናል። ምክንያቱም ሁሉን ትተን፣ የርሱ ደቀመዝሙር ለመሆን ራሳችንን ክደን፣ መስቀላችንን ተሸክመን የህይወትን ወንጌል ለፍጥረት ሁሉ ለማድረስ ሳይሆን ፡- እኛ እንድንበለጽግ ፣ ከሰው ሁሉ ልቀን እንድንታይ ኢየሱስን የተከተልን ከሆነ ወንጌሉን በጽሑፍ ደረጃ ባንቀይረውም (ያውም አታሚዎቹ ሌሎች ስለሆኑ) በኑሮአችን ግን የተገለበጠ ወንጌል እየኖርን መሆኑ ይታያል። ቃሉ ግን እንዲህ ይላል “ኢየሱስ ክርስቶስ ትናንትና ዛሬ እስከ ለዘላለምም ያው ነው።” ምናልባት ይህን ቃል የምንጠቅሰው አሁንም ከሥጋዊ ምኖቶቻችን አንጻር አስታከን ዳቦ ያበረከተው ጌታ አልተለወጠምና እኔንም ገንዘብ ይሰጠኛል ከሚል መንፈስ ነው። ነገር ግን ክርስቶስ የማይለወጥ መሆኑን ካመንን ትምህርቱም እንደማይለወጥ እንመን። ያ ሐዋርያቱን «ሁሉን ትታትችሁ ተከተሉኝ» ያለው ክርስቶስ ያ «ማንም ራሱን ቤተሰቡን ሚስቱን ልጆቹን አባቱን እናቱ የማይክድና መስቀሉን ተሸክሞ የማይከተለኝ የኔ ሊሆን አይችልም ያለው አሁንም አይለወጥም። የክርስቶስ ኢየሱስን የደቀ መዝሙር መለኪያ ዝቅ አድርገን ልናምንና ልናስተምር በጭራሽ መብትና ስልጣን የለንም። 

ክርስቶስ ደቀመዛሙርቱን ሁሉ የጠራውና መከተል የሌለባቸውንም የመለሰው በዚህ መለኪያ ነው። ህዝብ በዛ ብሎ ባየ ቁጥር መለኪያውን እንዳላወቁ አውቆ መለስ ብሎ ይነግራቸው ነበር “ብዙም ሕዝብ ከእርሱ ጋር ይሄዱ ነበር፥ ዘወር ብሎም እንዲህ አላቸው፦ ማንም ወደ እኔ የሚመጣ ቢኖር አባቱንና እናቱን ሚስቱንም ልጆቹንም ወንድሞቹንም እኅቶቹንም የራሱን ሕይወት ስንኳ ሳይቀር ባይጠላ፥ ደቀ መዝሙሬ ሊሆን አይችልም። ማንም መስቀሉን ተሸክሞ በኋላዬ የማይመጣ፥ ደቀ መዝሙሬ ሊሆን አይችልም።….. እንግዲህ እንደዚሁ ማንም ከእናንተ ያለውን ሁሉ የማይተው ደቀ መዝሙሬ ሊሆን አይችልም።” (ሉቃ.14:25) ኢየሱስ ብዙ ህዝብ በማየቱ ብቻ «አገልግሎቴ ብዙ ህዝብ አስገኘልኝ» ብሎ ደስ አላለውም። ይልቅስ የህዝቡ መብዛት ደቀመዝሙር የመሆን መለኪያውን አለማወቃቸው መሆኑን አውቆ ዘወር አለ። እርሱን ለመከተል መክፈል ያለባቸውንም ዋጋ ነገራቸው። ዛሬም በየአብያተ ክርስቲያናቱ ያለው የህዝብ መብዛት የደቀ መዝሙሮች ብዛት አለመሆኑን የጌታ መንፈስ ያብራልን። ይህም የሆነው ይህንን ኢየሱስ የሰበከውን ብቸኛ ወንጌል ባለመስበካችን ነው። ሌላ ወንጌል ሌላ ፍሬ ማፍራቱ አይቀርም። በውጤቱም ብዙ ህዝብ ቢኖርም ብዙ ደቀ መዝሙር የለም። የእኔነት የጥልና የክርክር ብዛት የመስቀሉ ወንጌል አለመኖር ምልክት ነው። መስቀል ያልተሸከሙ ብዙ ትክሻዎች ጥልን ክርክርን ለመሸከም ተጋልጠዋል።

ዛሬም ጌታ የርሱን ፈለግ በተከተሉ እውነተኛ አገልጋዮቹ ዘወር ብሎ እውነተኛውን የደቀመዝሙር መለኪያ ለህዝቡ እየተናገረ ነውና ስሙት አዎ ብዙ ከመድከማችን በፊት እንስማው። የነርሱ ደቀመዛሙርት እስከሆናችሁና የጸሎት ቤታቸውን ወንበር እስከሞላችሁ ድረስ የኢየሱስ ደቀመዛምርት ትሁኑ አትሁኑ የማይገዳቸው ምንደኛ አገልጋዮች ይህንን አይነግሯችሁም። እውነተኛው ጌታ ግን በከንቱ እንዳትደክሙ ቆም ብላችሁ ኪሳራችሁን እንድታስቡ ዘወር ብሎ እየተናገረ ነው። ጌታ የፈለገው ራሳቸውን ክደውና መስቀላቸውን ተሸክመው፣ ለራሳቸው መኖር አቁመው እርሱ የሚኖርባቸውን ታማኝ ደቀ መዛሙርት እንጂ የህዝብ ብዛትን አይደለም። ጌታ ኢየሱስ ይህ ስብከቱ ብዙ ጊዜ ብዙ ህዝብን ወደ ኋላ ቢመልስበትም መንገዱን አልቀየረም። ህጻናትና ሴቶች ሳይቆጠሩ አምስት ሺ ያህል ሰውን እንጀራ አበርክቶ ካበላ በኋላ በነበረው ቀን ያንን አገልግሎት እንዲቀጥልና ቢቀጥል ህዝብ እንደሚበዛለት አስበው ተጠራርተው የመጡትን ሰዎች አሳፍሮ የመለሰበት ያ ታሪካዊ ቀን አንመለስም ያሉ አስራ አንድ ታማኝ ደቀመዛሙርትን ብቻ ይዞ እንዲቀር አድርጎታል። 

ዛሬም የምናመልከውና የምናገለግለው ያ ኢየሱስ ከሆነ መንገዱ እንደዚያው ነው። እውነተኛ ደቀመዛሙርት ያልሆኑ፣ ለሚጠፋ መብል፣ ለኑሮ፣ ለብልጽግና ጌታን የሚፈልጉ ሁሉ ወደቤታቸው ሊሸኙ ይገባቸዋል። ቤተ ክርስቲያን ለእንደዚህ ዓይነት ሰዎች ጸሎት ቤት በመስራትና ወንበር በማሰራት እንዲሁም ሳምንታዊ ፕሮግራሞችን በማካሄድ ከንቱ ድካም መድከም የለባትም። በእውነት ወንጌል መለኪያ ወደ ቤታቸው ልትሸኛቸው ይገባል። ግን እንዴት እንሸኛቸው? ጸሎት ቤት በር ላይ ቆመን «አትምጡ» ብለን በመመለስ አይደለም ይልቅስ የሚፈልጉትን ምግብ በማሳጣት እንጂ። «ጌታ ይባርከኛል ፣መኪና፣ ቤት፣ ትዳር፣ ገንዘብ ይሰጠኛል» ብለው ሲመጡ ይህንን የሚያሳጣ ወንጌል በመስበክ ነው። ራሳቸውን ክደው መስቀላቸውን ተሸክመው ኢየሱስ ክርስቶስን ራሱን እየበሉና እየጠጡ እንዲከተሉት፣ ኢየሱስ ህይወታቸው እንዲሆን፣ መንፈስና ህይወት የሆነውን ቃሉን በየእለቱ እንዲመገቡ በመርዳት፡- ደቀመዝሙር ያልሆነውንና የኢየሱስ ወንጌል የማያረካውን ህዝብ ከአዳራሾቻችን መቀነስ አለብን።

ካሱ ቦስተን

እባክዎን ካነበቡ በኋላ ላይክ የሚለውን ይጫኑ እንዲሁም መልእክቱን ለሌሎች ያካፍሉ አመሰግናለሁ

ጎልጎታ !    የመስቀሉ ስፍራ !

ኢየሱስንም ይዘው ወሰዱት መስቀሉንም ትሸክሞ በእብራይስጥ ጎልጎታ ወደተባለው የራስ ቅል ስፍራ ወደሚሉት ወጣ (ዮሃንስ 19:17)

    ዛሬ በኢትዮጵያ ውስጥ በተለይም በመሃል አዲስ አበባ መስቀል አደባባይ ስፍራን ምክኒያት አድርጎ ለውዝግብና ለከፍተኛ የሰው መለያያ ወይም ሰዎችን በሃይማኖት ስም ጦርነት ማስከፈቻ ቅስቀሳ እየተሰራበት ያለ ትልቅ አጀንዳ ተይዞ ሊፈነዳ እያኮበኮበ ያለ ትልቅ የሃይማኖት ቦምብ የሚያከሽፈው የሃይማኖት አባት ካልተነሳ (ያውም ካለ ነው ምክኒያቱም አሁን የሃይማኖት አባቶች ከሚናገሩትና ከሚያስተምሩት ይልቅ ፖለቲካ ውስት ያሉ የአገር መሪዎች ሰውን የማረጋጋትና የማስታረቅ አገልግሎት እየታየ ስለሆነ) ይህ የሃይማኖት ቦምብ የፈነዳ እንደሆነ፤ ብዙ ሊያባራ የማይችል እልቂት እንደሚያስነሳ ከወዲሁ መገመት አያቅትም። ከአመታት በፊት የተፈጠረውን የቋንቋ እና የዘር መለያየትን ጥለን አንድ ወደመሆን እየመጣን ባለንበት ሰዓት በሃይማኖት ልዩነትን ማስነሳት ሊፈታ የማይችል ቁርሾ ሊያመጣ እንደሚችል ማወቅ አለብን። 

    በዚህ ዘመን ሰይጣን በሰዎች አይምሮ ውስጥ የራሱን ሃሳብ እየከተተ ሰውን ከሰው ጋር የሚያባላበትንና የሚያጨራርስበትን መንገድ በመቀየስ ላይ ነው። ወንድማማችነትን፤ ህብረትን፤ አንድነትን፤ መያያዝን፤ የማይፈልገው ሰይጣን አሁንም የአገራችንን ህዝብ ወደአንድነት መምጣት በመጥላት የተለያየ ሃሳብን እያመጣ ሲያነካክስና ሲያባላ ይታያል። ከአመታቶች በፊት ያለያየበትን የዘርና የቋንቋ  ልዩነትን ህዝቡ ነቅቶ በአንድነት ለመያያዝ ቋንቋና ዘር አይለየንም፤ በልዩነታችን አንድነታችንን አጠናክረን እንያያዝ፤ ባለበትና ለአንድነት በተነሳበት ሰዓት፤ይህንን ልዩነት ለማፍረስ እየሰራበት ያለውን ሃሳብ ልንነቃበት ያስፈልጋል።  

   ሰይጣን ሃሳቡን በሰዎች በተለይም በታዋቂ ሰዎች፤ ብዙ ህዝብ በሚከተላቸው ሰዎች ውስጥ እያስገባ ልዩነትን እየፈጠረ ሰዎችን ወንድማማቾችን፤ ቤተሰቦችን እንዲሁም ትዳርን ሁሉ ለማፍረስ እየጣረ ያለበት ጊዜ ነው። እባብ በተንኮሉ ሄዋንን እንዳሳታት ሃሳባችሁ ተበላሽቶ ለክርስቶስ ከሚሆን ቅንነትና ንጽህና ምናልባት እንዳይለወጥ ብዬ እፈራለሁ፤ ብሎ ሃዋርያው ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች እንደጻፈላቸው፤ እኔም በዚህ ዘመን እባብ በተንኮሉ ሃሳባችንን ሊያበላሽና ሊያስተን ለክርስቶስ ከሚሆን ቅንነታችንና ንጹህነታችን እንድንለወጥና የሱን ሃሳብ እንድናከናውን ሊያደርገን እንዲሁም እርስ በርስ እየተነካከስን እንድንጠፋፋ ሊያደርገን ነውና ዛሬ እንንቃበት፤ ልዩነታችን እንደተጠበቀ ሆኖ የሚያምረውን አንድነታችንን እንጠብቅ፤ ህብረታችንን እናጠናክር። 

    የመስቀሉ ስፍራ ጎልጎታ ነውና በዚያ በጎልጎታ ከመስቀሉ ላይ የወጣው ድምጽ “የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው የሚል ነው”፤ መስቀሉ ላይ ሰላም የተገኘበት፤ መስቀሉ ላይ ጥል ተገድሎ እርቅ የተገኘበት፤ መስቀሉ ላይ የአይሁድ ንጉስ የናዝሬቱ ኢየሱስ የሚል ጽሁፍ የሰፈረበት፤ መስቀሉ ላይ ለሰው ልጆች ሃጢዓት ዋጋ ያውም የንጹህ የክርስቶስ ደም የተከፈለበት፤ መስቀሉ ለሚጠፉት ሞኝነት ሆኖ ለሚድኑት ግን የእግዚአብሄር ሃይል የሆነበት፤ መስቀሉ እግዚአብሄር ሰውን ከራሱ ጋር እንዲሁም ሰውን ከሰው ጋር ያስታረቀበት፤ መስቀል የሰው ትምክህት የተወገደበት፤ መስቀል ጨለማ ተገፎ ብርሃን የወጣበት፤ መስቀል በሰዎች ላይ የተጻፈውን እና ሰውን ወደፊት እንዳይራመድ በመንገዱ ላይ ብቅ እያለ አላስኬድ ያለውን የእዳ ጽህፈት ተደምስሶ ከመንገዱ የተወገደበት ነው። 

    መስቀል ሽክማችንን እና ቶሎም የሚከበንን ሃጢያትን ሁሉ የምናስወግድበት እንዲሁም የእምነታችንን ራስና ፈጻሚ የሆነውን ኢየሱስን እየተመለከትን በፊታችን ያለውን ሩጫ በትእግስት የምንሮጥበት መንገዳችንም ነው። 

    ስለዚህ ወገኔ ዛሬ ልናስተውል የሚገባን የክርስቶስ መስቀል እኔና አንተ አንቺ የምንዋጋበት የምንጋደልበት ደማችንን የምናፈስበት ሳይሆን ሰላምና እርቅን ፈጥረን በአንድነትና በህብረት ዓይናችንን በመስቀሉ ላይ ወደተሰቀለው ክርስቶስ በማድረግ የመስቀሉን ስፍራ ጎልጎታን በምናባችን እያየን የምንጓዝበት ጊዜ እናድርገው። ሃዋርያው ጳውሎስ እንደጻፈልን በሰይጣን እንዳንታለል የርሱን ሃሳብ አንስተውምና እንዳለን እናም የርሱን ሃሳብ እንንቃበት። 

    መስቀሉ የምንጣላበት የምንጋደልበት ሳይሆን በአንድነት በህብረት የመስቀሉ ሃይል ለሰው ልጆች ሁሉ እንደሆነ፡ በመስቀሉ ላይ የተሰራውን እየመሰከርን ሰውን ከእግዚአብሄር ጋር እና ሰውን ከሰው ጋር የምናስታርቅበት ይሁንልን፤ መስቀል ሰላማችን ነውና። አሜን! 

ካሱ ቦስተን 

እባክዎን ካነበቡ በኋላ ላይክ የሚለውን ይጫኑ እንዲሁም መልእክቱን ለሌሎች ያካፍሉ አመሰግናለሁ

በድምጽ (በጉሮሮ) ላይ ተጽዕኖ የሚያመጡ መጠጦች

ይህ ጽሁፍ ረጅም ሰዓት ለሚያስተምሩና ለሚዘምሩ ወገኖች በድምጽ (በጉሮሮ) ላይ ተጽዕኖ ሊያመጣባቸው ይችላል በሚል ሊወገዱ የሚገባቸው መጠጦች ከብዙዎቹ በጥቂቱ እነዚህ ናቸው ተብሎ ይታሰባል

1. አረንጓዴ ሻይ (green tea ) – ይህ ድምጽ የሚፈጠርባቸው አካባቢዎችን የማድረቅና የመሰነጣተቅ ባህሪ ስላለውና በተፈጥሮ በተለያዩ የውስጥ ሰውነታችን ላይ ያለውን እርጥበት እንዲቀንስ ስለሚያደርግ እንዳይጠጣ ይመከራል::

2. ወተት (milk ) – ወተት በጉሮሮአችን እና በአፍንጫችን መንገድ ላይ ከፍተኛ የወፍራም ምራቅ ወይም (አክታ) ክምችትን ስለሚያስከትል ለድምጽ አወጣጥ ላይ ከፍተኛ ችግር ይፈጥራል ተብሎ ይገመታል::

3. የበረዶ ውሃ (Ice cube/chips) – የቀዘቀዘ ውሃ እየጠጣን ማስተማርም ሆነ መስበክ ወይም መዘመር ለድምጽ መልካም ያልሆነበት በድምጽ መፈጠሪያ አካባቢ ያሉ ጡንቻዎች በቅዝቃዜ ስለሚኮማተሩና ድምጽ ለማውጣት ያለው ጫና እንዲሰነጣጠቁ ያደርጋቸዋልና የሞቀ ሻይ ቢጠጣ (preferably peppermint or licorice root tea; both are fabulous.) መልካም እንደሆነ ይመከራል

4. ጋዝ ያላቸው መጥጦች(ኮካ ፔፕሲ አምቦ ውሃ … ) እነዚህ መጠጦች በሆዳችን ውስጥ ጋዝ ማለትም አየር ይፈጥርና እየሰበክንም ይሁን እየዘመርን ከሆዳችን ውስጥ በከፍተኛ ግፊት ወደ ድምጽ ማውጫ ጉሮሮ ይመጣና በድምጽ አወጣጥ ላይ ችግር ይፈጥርብናል እንደገናም የሆዳችንን ጡንቻ ዘና አድርገን በዲያፍራም የሳምባ ጡንቻ ብቻ እየተነፈስን እንዳናስተመር/እንዳንሰብክ ወይም እንዳንዘምር ያደርጉናል::

ካሱ ቦስተን

እባክዎን ካነበቡ በኋላ ላይክ የሚለውን ይጫኑ እንዲሁም መልእክቱን ለሌሎች ያካፍሉ አመሰግናለሁ

እጅግ ወዳለችና ብዙ ኃጢያቷ ተሰርዮላታል

አንድ ቀን ከፈሪሳውያን አንዱ ኢየሱስን በቤቱ ምሳ እንዲበላ ለመነውና ወደ ቤቱ ገባ። «እነሆም በዚያች ከተማ ኃጢአተኛ የነበረች አንዲት ሴት፤ በፈሪሳዊው ቤት በማዕድ እንደ ተቀመጠ ባወቀች ጊዜ፥ ሽቱ የሞላበት የአልባስጥሮስ ቢልቃጥ አመጣች። በስተ ኋላውም በእግሩ አጠገብ ቆማ እያለቀሰች በእንባዋ እግሩን ታርስ ጀመረች፥ በራስ ጠጕርዋም ታብሰው እግሩንም ትስመው ሽቱም ትቀባው ነበረች።» (ሉቃ.7፡37-38) በዚህን ጊዜ ይህ ፈሪሳዊ በልቡ «ይህስ ነቢይ ቢሆን፥ ይህች የምትዳስሰው ሴት ማን እንደ ሆነች እንዴትስ እንደ ነበረች ባወቀ ነበር፥ ኃጢአተኛ ናትና ብሎ በልቡ አሰበ።» በማለት አሰበ። ኢየሱስም የልቡን ሐሳብ አወቀና እንዲህ ሲል በምሳሌ አስረዳው «ኢየሱስም መልሶ፦ ስምዖን ሆይ፥ የምነግርህ ነገር አለኝ አለው። እርሱም፦ መምህር ሆይ፥ ተናገር አለ። ለአንድ አበዳሪ ሁለት ተበዳሪዎች ነበሩት በአንዱ አምስት መቶ ዲናር ነበረበት በሁለተኛውም አምሳ። የሚከፍሉትም ቢያጡ ለሁለቱም ተወላቸው። እንግዲህ ከእነርሱ አብልጦ የሚወደው ማንኛው ነው? ስምዖንም መልሶ፦ ብዙ የተወለቱ ይመስለኛል አለ። እርሱም፦ በእውነት ፈረድህ አለው።ወደ ሴቲቱም ዘወር ብሎ ስምዖንን እንዲህ አለው፦ ይህችን ሴት ታያለህን? እኔ ወደ ቤትህ ገባሁ፥ ውኃ ስንኳ ለእግሬ አላቀረብህልኝም፤ እርስዋ ግን በእንባዋ እግሬን አራሰች በጠጕርዋም አበሰች። አንተ አልሳምኸኝም፤ እርስዋ ግን ከገባሁ ጀምራ እግሬን ከመሳም አላቋረጠችም። አንተ ራሴን ዘይት አልቀባኸኝም፤ እርስዋ ግን እግሬን ሽቱ ቀባች። ስለዚህ እልሃለሁ፥ እጅግ ወዳለችና ብዙ ያለው ኃጢአትዋ ተሰርዮላታል፤ ጥቂት ግን የሚሰረይለት ጥቂት ይወዳል። እርስዋንም። ኃጢአትሽ ተሰርዮልሻል አላት። (ሉቃ.7፡40-48)
          በዚህ አስደናቂ ታሪክ ውስጥ ወደ ኢየሱስ የምንቀርብበት አቀራረብ ምን እንደሚመስል። የሰው ሐሳብና የእግዚአብሔር ሐሳብ ምን ያህል የተራራቀ እንደሆነ። አሁንም በዚህች ቅጽበት ወደ ጌታ እየቀረብንበት ያለውን መንገድ እንድንፈትሽ ለማየት እንችላለን።
ለመሆኑ በዚህ ስፍራ ካሉት ሁለት ኢየሱስን ተቀባዮች የትኛውን ትመስላለህ? ትመስያለሽ? ይህንን ጥያቄ ለመሆን የምንፈልገውን ከማሰብ አንጻር ሳይሆን አሁን ጌታን እያስተናገድንበት ካለው እውነተኛ ገጽታ አንጻር ብንመልሰው የበለጠ ተጠቃሚ እንሆናለን። መልሳችን መሆን ያለበት በውድድር እንዳለ ሰው ነጥብ ከማስቆጠር አንጻር ሳይሆን ከጌታ ጋር ያለንን ህብረት ፈትሸን ከማስተካከል አንጻር ይሁን።
        እነዚህ ሰዎች ሁለቱም ወደ ጌታ ቀርበዋል ሁለቱም ጌታን ፈልገውታል። የፈለጉበት ልብና የቀረቡበት አቀራረብ ግን የተለየ ነው። ይህም በውጤቱ ላይ ለውጥ አምጥቶአል። እንደሰው ስናየው በአግባቡና በስርአቱ ያስተናገደውና የተቀበለው ፈሪሳዊው ነው። በክብር ምሳ ጋብዞታል። የጋበዘውም ወደ ሌላ ሰው ቤት ሳይሆን ወደራሱ ቤት ነው። ኃጢአተኛዋ ሴት ግን ይህን ሁሉ አላደረገችም። ኢየሱስ በፈሪሳዊው ቤት እንደተቀመጠ ባወቀች ጊዜ እንዲሁ ሳትጠራና ሳትጋበዝ መጣች። ይህ ፈሪሳዊ ለኢየሱስ እያደረገ ያለው የሚቆጠር የሚመካበት ነገር አለው። ይህች ሴት ግን ምንም የምትመካበትና የምትቆጥረው ነገር የላትም። ጌታን ወደቤትዋ አልጋበዘችውም (እንደሚመስለኝ በዝሙት የምትተዳደር ሴት ከሆነች ከዝቅተኛው ህብረተሰብ ስለምትመደብ ሰው የምትጋብዝበት ቤትም ያላት አይመስለኝም) ነገር ግን ራስዋን አዋርዳ ወዳልተጠራችበት ቤት ወዳልተጋበዘችበት ቤት መጣች። ለሰው ወዳልተጋበዙበት ግብዣ መሄድ የሚያሳፍር ነው። የሚገርመው ደግሞ የመጣችበት ቤት ለእንደርስዋ አይነት ሴት የማይሆን የፈሪሳዊ ቤት ነው። ይህ ፈሪሳዊ እርስዋን እንዴት እንደሚመለከታት ታውቃለች። ኃጢአተኛ ስለሆነች በህጉ አይን ነው የሚመለከታት። እንድትወገርና እንድትሞትም ሊያመቻች ይችላል። ስለዚህ ኢየሱስን አምና መጣች እንጂ እንደሰው ሲታይ ወደ ሞት ቀጠና ነው የመጣችው። ወንጀል ይዞ ፓሊስ ጣቢያ መሄድን ማን ይፈልግና። ወደዚህ ቤት እንድትመጣ ያስገደዳት ግን ከዚያ ከሚፈርድባትና እስከሞት ድረስ ከሚያሳድዳት በልጦ የነገሰው የዓለም ብርሃን ስለታያት ነው። «ብርሃንም በጨለማ ይበራል፥ ጨለማም አላሸነፈውም።» (ዮሐ.1፡5) ተብሎ እንደተጻፈ በዚያ ድሮ ሞትና ፍርድ ብቻ ነግሶ በሚታይበት የፈሪሳዊ ቤት ይህ ብርሃን አሸንፎ ታያት። ይህን ብርሃን ተማምና ወደዚያ ጨለማ መንደር ገባች።

        ስለዚህ አቀባበላቸውን ስናይ የፈሪሳዊው ደረጃውን የጠበቀ ሲሆን የርስዋ ግን «ድንኳን ሰባሪ» እንደሚባሉት ህገ ወጥ የሚባል ነው። ይህ ፈሪሳዊ የሰራው ነገር ክፉ የሚባል ሳይሆን መልካም የሚባል ነው። ሌሎች ፈሪሳውያን ጌታን ለመግደል ሲያሳድዱትና በቃል ሊያጠምዱት ሲከታተሉት እርሱ ግን ወደ ቤቱ ጠርቶ ምሳ መጋበዙ ትንሽ ነገር አይደለም። ሌሎች ምን ይሉኛል አለማለቱም ያስመሰግነዋል። ኢየሱስን የጋበዘው ግን ማንነቱን አውቆ ሳይሆን ማንነቱን ለማወቅ እንደሆነ እናያለን። የተቀበለው አቀባበል ሰፍ ያለ ሰው አቀባበል አለመሆኑና ይህች ሴት በምትዳስሰው ጊዜ በልቡ ያሰበው ነገር ይህንን ፍንትው አድርጎ ያሳየናል። «ይህስ ነቢይ ቢሆን፥ ይህች የምትዳስሰው ሴት ማን እንደ ሆነች እንዴትስ እንደ ነበረች ባወቀ ነበር፥ ኃጢአተኛ ናትና ብሎ በልቡ አሰበ።» (ሉቃ.7፡39) ይላል። ስለዚህ ነቢይ ይሁን አይሁን ለመለየት ነበር የጠራው አሁን ማረጋገጫውን አገኘ ማለት ነው። እውነተኛው ረቢ ኢየሱስ ግን ባልጠበቀው መንገድ ሚስጢሩን ይተርክልት ጀመር። በእውነት ኢየሱስ እውነተኛ ረቢ ነው። ምሳ ተጋብዣለሁ ብሎ እውነትን የማይደብቅ ለራሱ ሊኖር ያልመጣ ከሰማይ የሆነ ሰው በመሆኑ በሰው ልጆች መንደር የተለመደው ምን ይሉኛል ያልነካካው። ለእውነት ሊመሰክር የተወለደ። ራሱ እውነት ሆኖ እውነትን ያስተማረ ድንቅ ረቢ።

    «እግዚአብሔር ሕዝቤን ስለሚያስቱ ነቢያት እንዲህ ይላል በጥርሳቸው ሲነክሱ በሰላም ይሰብካሉ በአፋቸው ግን አንዳች በማይሰጥ ሰው ላይ ሰልፍን ያስቡበታል።» (ሚክ.3፡5) የተባለላቸው ሐሰተኞች በሞሉበት ዘመን ምሳ በልቶ እውነትን የሚናገርና የሚገሰጽ እውነተኛ እረኛ እግዚአብሔር ለህዝቡ ሰጠ። በዚህ ዘመን ያሉ «ስለ ጭብጥ ገብስና ስለ ቍራሽ እንጀራ» (ህዝ.13፡19) ህዝብን የሚያረክሱና ለሆዳቸውና ለኪሳቸው ያደሩ አገልጋዮች ከዚህ ድንቅ መምህር ፍለጋን ይማሩ ዘንድ ይገባል። ይህ ድንቅ መምህር በክብር ምሳ የጋበዘውን ሰው ወደ ቤቱ እንጂ ወደ ልቡና ወደ ህይወቱ እንዳልጋበዘው እንዲህ በማለት አስረዳው «ወደ ሴቲቱም ዘወር ብሎ ስምዖንን እንዲህ አለው፦ ይህችን ሴት ታያለህን? እኔ ወደ ቤትህ ገባሁ፥ ውኃ ስንኳ ለእግሬ አላቀረብህልኝም፤ እርስዋ ግን በእንባዋ እግሬን አራሰች በጠጕርዋም አበሰች። አንተ አልሳምኸኝም፤ እርስዋ ግን ከገባሁ ጀምራ እግሬን ከመሳም አላቋረጠችም። አንተ ራሴን ዘይት አልቀባኸኝም፤ እርስዋ ግን እግሬን ሽቱ ቀባች። (ሉቃ.7፡44-46) ዋው ይህ አክብሮ ምሳ ለጋበዘ ሰው እጅግ መራራ እውነት ነው። ግን እየመረረ የሚፈውስ መድኃኒት። 

      ዛሬም እንዲህ እላለሁ እግዚአብሔር ሆይ እየመረረንም ቢሆን እውነትን የሚነግሩንን እረኞችና አስተማሪዎችን አስነሳልን ይህ ይሻለናል።  

                   አሜን ይሁንልን !!! 

ካሱ ቦስተን

እባክዎን ካነበቡ በኋላ ላይክ የሚለውን ይጫኑ እንዲሁም ሌሎች ዌብሳይቶቼን ከታች በሚገኘው ሊንክ ያግኙታል አመሰግናለሁ

እናንተ የምድር ጨው ናችሁ !

እናንተ የምድር ጨው ናችሁ፤ ጨው አልጫ ቢሆን ግን በምን ይጣፍጣል? ወደ ውጭ ተጥሎ በሰው ከመረገጥ በቀር ወደ ፊት ለምንም አይጠቅምም። (ማቴዎስ 5፡13)

      የሰው ልጅ ጨውን ለብዙ መቶ ሺህ ዓመታት ለተለያየ አገልግሎት ሲተቀምበት ኖሯል አሁንም እየተጠቀመበት ይገኛል፡፡  ጨው በዓለም ላይ የሰው ልጅ ከተፈጠረበት ጊዜ ጀምሮ ከ14,000 በላይ ለሚሆኑ የተለያዩ አገልግሎቶች መዋሉን ሰለጨው ጥቅሞች በተለያዩ ድህረገጾች ላይ ተገልጾ ይገኛል፡፡ 

 ስለጨው ጥቅምና ጉዳት ለመዘርዘር ሳይሆን ለምንድነው ጌታ እኛን በጨው የመሰለን ? ለዚያውም የምድር ጨው ናችሁ ሲለን ምን ለማለት ፈልጎ ነው?  የሚለው ነጥብ ላይ ማተኮር ያስፈልገናል ስለዚህ በትንሹ ጨው ለምግብ ከሚሰጠው ጥቅም ጋር አያይዘን እንመልከተው ፡፡ 

ምግብ ለመበላት ሊጣፍጥ ይገባዋል፡፡ ምግብ የማይጣፍጠው ከሆነ ሰው ለመብላት አይበረታታም፡፡ ምግብን ለማጣፈጥ የሚጠቅመው ዋነኛው ነገር ደግሞ ጨው ነው፡፡ ጨው የምግብ ጣእምን ሰብሰብ የማድረግ አቅም አለው፡፡ ጨው የምግብ ጣእምን ወደ አንድ ደረጃ የማምጣት ችሎታ አለው፡፡  ጨው ምግቦችን ጣዕማቸው ሳይቀይር የማቆየት ብቃት አለው፡፡ ጨው የሚስብ ነገር አለው፡፡ ጨው በሁሉ ሰው ታዋቂና ተፈላጊ ጣእም አለው፡፡ ጨው በሁሉም አይነት ምግቦች ላይ ቀይ ወጥ: አልጫ ወጥ: ጎመን ወጥ: ሰላጣ: ፍርፍር: ወ.ዘ.ተ. ጨው የማይገባባቸው የምግብ አይነቶች የሉም፡፡ ምንም ያህል ድግስ ተደግሶ የሚያጣፍጥ ጨው ከሌለው ድግሱ ተመጋቢ ያላገኘ ድግስ ይሆንና የተዘጋጀው ምግብ ወደቆሻሻ መጣያ ስፍራ መወሰዱ አይቀሬ ነው ፡፡ ልክ ከእግዚአብሄር ጋር በክርስቶስ የመስቀል ስራ እንደታረቅን ወደ መንግስተ ሰማያት ያልገባነው በምድር ላይ ወሳኝ ስራ ስላለን ነው፡፡ ስለ   እኛ ስለተከታዮቹ ኢየሱስ ሲናገር የምድር ጨው ናችሁ ይላል፡፡

     ጨው የምግብን ደረጃ ከፍ እንደሚያደርገው እኛ የምድርን የህይወት ደረጃ ከፍ እናደርገዋለን፡፡ እኛ እግዚአብሄርን የመፍራት ከፍ ያለ የህይወት ደረጃ ካላሳየን ምድር እግዚአብሄርን ፈርቶ የሚያስፈራራው ምሳሌ አይኖረውም፡፡ እግዚአብሄርን የመምሰል ህይወት ምሳሌ ካልሆንን ምድር የእግዚአብሄርን መልክ ማየት አትችልም፡፡ እኛ እግዚአብሄርን ስለማክበር ሞዴል ካልሆንን አለም እግዚአብሄር እንዴት እንደሚከበር ምንም ፍንጭ አይኖረውም፡፡ በእግዚአብሄር ፀጋ በራስ የማይቻል ነገር በማድረግ እግዚአብሄር እንዳለ ካልመሰከርን ስለእግዚአብሄር መኖር የሚመሰክር ሰው አይኖርም፡፡ 

ጨው የምግብን የተለያየ ጣእም እንደሚሰበስበውና አንድ ወጥ ጣእም እንደሚሰጠው እኛም የምድርን ትኩረት ወደ ሰማይ የምናመለክተው እኛ ነን፡፡ እንዲሁም ከሞት በኋላ ህይወት አንዳለ አድርገን በመኖር ሌሎችንም የምናነቃውና ምድራዊ ህይወት ጊዜያዊ እንደሆነ አድርገን በመኖር ሌሎቹ ለዘላለማዊ ህይወት እንዲዘጋጁ የምናስጠነቅቀው እኛ ነን፡፡ በሰማይ ጌታ እንዳለው ሰው በመኖር ራስን በመግዛትና በዲሲፒን ኑሮ ክርስትና እንደሚቻል ፣ እግዚአብሄርን ማስደሰት እንደሚቻልና ለእግዚአብሄር ሙሉ ለሙሉ መኖር እንደሚቻል ለሌሎች ምሳሌ የምንሆነው እኛው ነን፡፡

    ሰው በእግዚአብሄር አምሳል እንደተፈጠረና ለእግዚአብሄር ክብር እንደተሰራ በህይወታችን የምናመለክተው እኛ ነን፡፡  እግዚአብሄርን ማክበር የሰው በምድር ላይ የመፈጠር አላማ መሆኑን የምናስታውሰው እኛ ነን፡፡ ምድርን ከሚታይ ነገርና ከስጋዊ ፍላጎት ከፍ ያለን ደረጃ የምንሰጣት እኛ የምድር ጨው ነን፡፡ በምድር ላይ የእግዚአብሄር ልጅ ሆኖ ስለመኖር ለሌሎች የምንመሰክረው እኛ ነን፡፡ በምድር ላይ እግዚአብሄርንና ሰውን በመውደድ እንዴት እንደሚኖር የምንመሰክረው እኛ ነን፡፡

    ጨው ክብሩ ለምግብ ጣእም መስጠቱ ነው፡፡ የጨው ክብሩ ኮስታራነቱ ነው፡፡ እኛ ነን አለምን ማጣፈጥ የምንችለው፡፡ አለምን ለማጣፈጥ ጣእሙ ያለን እኛ ነን፡፡ እኛ ግን ይህንን ወሳኝ ሃላፊነታችንን ካልተወጣን ማንም ሊሰራልን አይችልም፡፡ እኛ አለምን ካላጣፈጥን እኛን ሊያጣፍጠን የሚችል አለም የለም፡፡ ጨው ደግሞ ካላጣፈጠ ለምንም አይጠቅምም፡፡

    ስለዚህ ነው ጨው በአለም ሁሉ መበተን ያለበት፡፡ ጨው በጨው እቃ ውስጥ ቢቀመጥ ምንም እንደማይጠቅም ሁሉ እኛም በየሰንበቱ መሰባሰባችንና ክርስትና ክርስትና ማለታችን ለሌላው ካልጠቀመ በጨለማው ላይ ካላበራና ለመራራው አለም ጣዕም ካልሰጠ ጠቃሚነቱ የማይታየው፡፡ ጨው ግን በተለያየ አይነት ወጥ ውስጥ ቢጨመር ያጣፍጣል ምግብ በሰሃን ተቀምጦ አጠገቡ በጠርሙስ ጨው መቀመጡ ምግቡን ሊያጣፍጠው እንደማይችል ነገር ግን  ከጠርሙሱ ውስጥ ወጥቶ ሊበተን እና ሊነሰሰነስ ይገባዋል ፡፡ ስለዚህ ክርስትያኖች የምንሰበሰበው ለመበረታታት ፣ ለመሞረድ ፣ ለመታደስ እና ለስራ ዝግጁ ሆነን ለመበተን እንጂ ስራው በምድር ፖለቲካ ፣ ኢኮኖሚና ማህበራዊ ህይወት ውስጥ ነው፡፡ ጨውነታችን በትምህርት ቤት ፣ በሆስፒታል ፣ በየፋብሪካውና በየኢንዱስትሪው በየስራ ስፍራችና በየሰፈራችን፣ በሃገር አስተዳደር ፣ በውትድር ፣ በንግድና በመሳሰሉት ሙያዎች ሁሉ ይፈለጋል፡፡

    እናንተ የምድር ጨው ናችሁ፤ ጨው አልጫ ቢሆን ግን በምን ይጣፍጣል? ወደ ውጭ ተጥሎ በሰው ከመረገጥ በቀር ወደ ፊት ለምንም አይጠቅምም። ማቴዎስ 5፡13

    ክርስትናን ካለራስ ወዳድነት በፍቅር ለሌሎች መልካም ምሳሌ በመሆን ክርስትናን እንዲቀበሉ የምናበረታታው የምድር ጨው በመሆን ነው፡፡ ስለዚህ መንፈሳዊ ቤት ሆኖ መሰራት አንዱ ለዚህ መራራ ለሆነው አለም ጣዕም ለመስጠት ነውና  እንግዲህ እኛ የምንጠቀምበት ጨው ጨው ሆኖ ከማገልገሉ በፊት ብዙ ሂደቶችን አልፎ ነውና ለማጣፈጫነት የዋለው እኛም አለምን ለማጣፈጥ በእግዚአብሄር ቃልና በጸሎት እንዲሁም በሃይሉ ችሎት እየበረታንና እየተሰራን እንድንዘጋጅ መሰራታችንን እንቀጥል እላለሁ ተባረኩልኝ።

ካሱ ቦስተን 

እባክዎን ካነበቡ በኋላ ላይክ የሚለውን ይጫኑ እንዲሁም መልእክቱን ለሌሎች ያካፍሉ አመሰግናለሁ

thelastbelldotcom.wordpress.com

kasselsa97

https://youtu.be/LbCx7WVy3ZY

https://www.tiktok.com/@kassuboston

linkedin.com/in/kassuboston

መሪና ተባባሪ

በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ከሚገኙ የመሪና የተባባሪ ድርሻን ከሚገልጡ ታሪኮች አንዱ የሙሴና፣ የአሮንና የሖር ታሪክ ነው(ዘጸ. 17÷8-16)፡፡

    አማሌቃውያን ከእስራኤል ጋር ሲዋጉ ኢያሱ ጎልማሶቹን ይዞ ከአማሌቃውያን ጋር ይዋጋ ነበር፡፡ ሙሴ ደግሞ ወደ ኮረብታው ወጣ፡፡ ሙሴ እጁን ባነሣ ጊዜ እስራኤል ድል ያደርጋሉ፡፡ ሙሴ ደክሞት እጁን ባወረደ ጊዜ ደግሞ አማሌቅ ድል ያደርጋሉ፡፡ በዚህ ሁኔታ ሙሴ ቀኑን ሙሉ ዋለ፡፡ በመጨረሻ ግን የሙሴ እጆች ከበዱ(ደከሙ)፡፡ ይህን የተመለከቱት አሮንና ሖር ለሙሴ የድንጋይ ወንበር አዘጋጁለት፤ ሙሴም እዚያ ድንጋይ ላይ ተቀምጦ እጁን ዘረጋ፡፡ ድሉም ለእስራኤል ሆነ፡፡ ነገር ግን አሁንም ሙሴ እጆቹ እየደከሙ መጡ፡፡ አሮንና ሖርም በግራና በቀኝ ሆነው የሙሴን እጆች ከፍ አድርገው ደገፏቸው፡፡ ያን ጊዜ ሙሴ እጆቹን አነሣ፡፡ እስራኤልም አማሌቅን ፈጽመው ድል አደረጉ፡፡

    አንድ መሪ ውጤታማ የሚሆው ብቻውን አይደለም፡፡ እንኳንና በሰዎች የተመረጠ መሪ እግዚአብሔር የመረጠው ሙሴ እንኳን ብቻውን ውጤታማ መሆን አልቻለም፡፡ መሪ ምን ጠቢብ፣ ጎበዝ፣ ውጤታማ፣ ተወዳጅና ዐቅም ያለው ቢሆንም እንኳን እንደ ሙሴ እጆች መዛሉ አይቀሬ ነው፡፡ ስለዚህም እንደ አሮንና እንደ ሖር መንገዱን አይቶ የሚደግፈው ይፈልጋል፡፡ መልካም መሪ ውሳኔዎቹ፣ የለውጥ ሐሳቦቹ፣ ዕቅዶቹና ቃል ኪዳኖቹ ተግባራዊ እንዲሆኑ የሚያበረቱት እንደ አሮንና ሖር የመሳሰሉ አጋዦች ያስፈልጉታል፡፡ አሮንና ሖር ለሙሴ የተሰጠው ሃላፊነት ወይም ራዕይ አልተሰጣቸውም፡፡ ነገር ግን ሙሴን ደግፈው የሚፈልጉትን ውጤት አመጡ፡፡ ሁሉም ሰው መሪ ባይሆንም የመልካም መሪን ሐሳብ፣ ዕቅድ፣ ራእይና ውሳኔ በመደገፍ ግን ለውጥ ማምጣት ይችላል፡፡

    ሙሴ አንድ ሲሆን ደጋፊዎቹ ግን ሁለት ነበሩ፡፡ ምንጊዜም ከደጋፊዎች ተደጋፊዎች ያንሳሉ፡፡ ታሪክ እንደሚያስተምረን ዓለምን የለወጧት ጥቂት ባለ ተሰጥዖዎች ናቸው፡፡ ነገር ግን ሐሳባቸውን፣ መንገዳቸውን፣ አመራራቸውን፣ ትምህርታቸውን፣ ጥረታቸውን የሚደግፉ አካላቶች ነበሯቸው፡፡  በቤተክርስቲያንም መርሁ አንድ ነው የቤተክርስቲያን መሪዎች እንዲሁም የየአገልግሎት ክፍል መሪዎች ሊደገፉ አይዞአችሁ ሊባሉ ከጎናችሁ ነን ሊባሉ ይገባቸዋል፡፡ መሪዎች ወይም ቤተክርስቲያንን ወደታየላት ግብ ለማድረስ ራዕይ ተቀብለው የሚንቀሳቀሱ ባለራዕዮች ስኬታማ የሚሆኑት የአገልግሎት ክፍሎች፣ በተለያየ ጸጋ የሚያገለግሉ አገልጋዮች፣ እንዲሁም ምዕመናን፣ ማግኘታቸው መሆኑን ልንዘነጋው አይገባንም፡፡

     ብዙ ሙሴዎች እንደ አሮንና ሖርን የመሰሉ አጋዦች አጥተው እጃቸው ዝሎ ድል ሆነዋል፡፡ መንገዱ፣ ሐሳቡ፣ ውጣ ውረዱ፣ ሙግቱ፣ ጭቅጭቁ፣ የሰው ትችትና ወቀሳ፣ ስድብና ዕንቅፋትነት አዝሏቸው ድል ከማድረግ ድል ወደመሆን ወርደዋል፡፡ በህይወት ዘመናችን ብዙ ሙሴዎች ተሰጥተውን ነበር፡፡ነገር ግን የሚያግዛቸውና ክንዶቻቸውን የሚደግፍ፤ ቢያንስ የድንጋይ መቀመጫ እንኳ የሚሰጥ አጥተው በሞትና በሽፈት ድል እየሆኑ ተገቢውን ለውጥ ሳያመጡ ቀርተዋል፡፡ ኧረ እንደውም ድንጋዩን እንዲቀመጡበት ከማድረግ ይልቅ ድንጋዩን እየወረወርን የፈነከትናቸው ስንቶች ይሆኑ ?

      ድል የማድረጊያ አንዱ መንገድ ብርቱዎቹን መደገፍ ነው፤ ክንዳቸው፣ ድምጻቸው፣ ሥራቸው፣ ጥረታቸው፣ ሐሳባቸው፣ ራዕያቸው ከፍ ሲል ድል እንዲያደርጉ መደገፍ ነው፡፡ መጥፎ ሠሪዎችን የምንቃወመውን ያህል መልካም ሠሪዎችን የማንደግፍ ከሆነ ውጤት አናመጣም፡፡

የሙሴም ታላቅነት ምን መሪ ቢሆን፣ እጆቹ ታላቅ ሥራ የሚሠሩና ድል አድራጊ ቢሆንም ሊደክም፣ ሊሸነፍ፣ ሊያቅተውና ሊዝል እንደሚችል አመነ፡፡ ያለ ሌሎች ድጋፍ ብቻውን ለውጥ እንደማያመጣ ተቀበለ፡፡ ታላቅነት ማለት የታናናሾችን አስተዋጽዖ መናቅ አይደለም፡፡ ሁሉን ብቻዬን አደርገዋለሁ አላለም፡፡ አሮንና ሖር እንደሚያስፈልጉት ተቀበለ፡፡ ጎበዝ ሰው እንዲህ ነው፡፡ ሁሉንም ለብቻዬ እችለዋለሁ አይልም፡፡ የአንድ ሰው ውጤታማነት የብዙ ሰዎች አስተዋጽዖ ውጤት ነውና፡፡ ድል የሙሴም፣ የአሮንና የሖርም የየብቻ ውጤት አይደለም፡፡ ድል የሙሴ፣ የአሮንና የሖር የኅብረት ውጤት ነው፡፡ ስለዚህ በፍቅር በህብረት ለድል እጅ ለእጅ እንያያዝ አሜን፡፡

በዚህ እና በሌሎችም ጽሁፎች ተባርከው ከሆነ ገጹን ላይክ ቢያደርጉ አስተያየቶትንም ቢያሰፍሩልኝ ደስተኛ ነኝ አመሰግናለሁ።

ጆሮ ያለው ይስማ !

ይህ የመጨረሻው ደውል የተሰኘው ድህረ ገጽ የማንቂያ ደውል እንደሆነም ያስቡ !

  ካሱ ቦስተን 

    ይህንን ጽሁፍ ወደውት ከሆነ ላይክ በማድረግ እንዲሁም ድህረ ገጹን ሰብስክራይብ ቢያደርጉ ሌሎች ጽሁፎች ሲለቀቁ ወዲያው እንዲደርስዎት ይሆናል። ለሌሎች በማካፈልም የድርሻዎትን ይወጡ።

እንዲሁም ከታች ባሉት ሌሎች ዌብሳይቶች ላይ ያገኙኛል ሊንኩን በመጫን ይፈልጉኝ አመሰግናለሁ።

linkedin.com/in/kassuboston

https://www.instagram.com/kasselsa97

https://www.facebook.com/kasselsa97

thelastbell.com (ይህ የመጨረሻው ደውል ገጽ)

የእግዚአብሄርን ቤት ጓዳዎች እናፅዳ

በነህምያ ዘመን እንዲህ ሆነ፡፡ ነህምያ የኢየሩሳሌምን መፍረስና የበሮችዋን መቃጠል በሰማ ጊዜ እጅግ አዘነ አለቀሰም፡፡ ከዚያም ከንጉሡ ፈቃድ አግኝቶ ኢየሩሳሌምን ሊሰራ በመጣ ጊዜ ሶስት ጠላቶች ተነሱበት፡፡ “ሐሮናዊውም ሰንበላጥ ባሪያውም አሞናዊው ጦቢያ ዓረባዊውም ጌሳም በሰሙ ጊዜ በንቀት ሳቁብን፡፡ ቀላል አድርገውንም ይህ የምታደርጉት ነገር ምንድን ነው? በውኑ በንጉሡ ላይ ትሸፍቱ ዘንድ ትወዳላችሁን? አሉን፡፡” ይላል (ነህ.2፥19) ከዚህም ሌላ በብዙ ማስፈራራትና ዛቻ፣ በደብዳቤም በሰውም ኢየሩሳሌም እንዳትሰራ የነህምያን ልብ ለመስበር ሞክረዋል፡፡ ነህምያ ግን የአምላኩ እጅ ከርሱ ጋር ነበረችና ሥራውን ጨረሰ

    ይህ ሁሉ ከሆነ በኋላ ግን የኢየሩሳሌምን መሰራት ሲቃወም የነበረው ጦቢያ መኖሪያ ፍለጋ ወደ መቅደሱ አዘገመ። ኤልያሴብ ከሚባለው ካህን ጋር በመወዳጀትም በእግዚአብሔር ቤት ጓዳ ለመቀመጥ ቻለ፡፡ ነህምያ ስለዚህ ነገር ሲናገር እንዲህ ይላል“ከዚህም አስቀድሞ በአምላካችን ቤት ጓዳዎች ላይ ተሹሞ የነበረው ካህኑ ኤልያሴብ ከጦቢያ ጋር ተወዳጅቶ ለሌዋውያንና ለመዘምራን ….. እንደ ህጉ የተሰጣቸውን ለካህናቱም የሆነውን የማንሳት ቁርባን አስቀድሞ ያስቀመጡበትን  ታላቁን ጓዳ አዘጋጅቶለት ነበር፡፡» (ነህ.13፥4-6) ይህ መንፈሳውያን ለሆኑ ሁሉ ታላቅ መልእክት አለው፡- የኢየሩሳሌምን መታነፅና መታደስ በፅኑ ሲቃወም የነበረው ተቃዋሚ ጠላት ጦቢያ ከእግዚአብሔር ቤት ውስጥ  ታላቁን ጓዳ ሲያገኝና በዚያ ሲቀመጥ ለነህምያና ዛሬም የነህምያ መንፈስ ለሆነላቸው እንዴት የሚያሳዝንና የሚያበሳጭ ነው ! ያውም የተሰጠው ታላቁ ጓዳ እንደህጉ ለሌዋውያን ለመዘምራን ለበረኞች ለካህናት በአጠቃላይ ለመቅደሱና ለታላቁ ንጉሥ ለእግዚአብሔር አገልጋዮች የተዘጋጀው መብል የሚቀመጥበት የከበረው ቦታ ነበር፡፡ መብል በሚቀመጥበት ቦታ  ውስጥ የእግዚአብሔር ህዝብ ጠላት ተቀምጦ ነበር፡፡ (ሚል.3፥10)

   ዛሬም በዚህ ቃል ራሳችሁንና መቅደሳችሁን ማለትም እግዚአብሄርን ማምለኪያና ህብረት ማድረጊያ ስፍራዎቻችሁን እንዲሁም መንፈሳዊ ጓዳችሁን ፈትሹ፡፡ ከካህኑ ወይም ከሐሰተኛ አገልጋዮች ጋር ተወዳጅቶ የእውነት ዓምድና መሰረት በሆነው በእግዚአብሔር ቤት ጓዳ ውስጥ የተቀመጠውን የዘመኑን ጦቢያ ሃሰተኛና አስመሳዩን ንቁበት፡፡ ይህም የዘረኝነት የግለኝነት (ቤተክርስቲያንን እንደግል ንብረት ማየት) የመጣላት የመለያየትና የመከፋፈል ምክንያት የሆነው አሮጌው ሰው ነው ፡  

     በእግዚአብሔር ቤት ውስጥ በተለይ አሁንም ጦቢያ “አሮጌው ሰው” ገዝፎ የሚታየው በታላቁ የአገልጋዮች የመዘምራን የሌዋውያን ጓዳ ነውና ነህምያዎች ሆይ ይህንን ጓዳ ለማፅዳትና ለእግዚአብሔር ለመቀደስ “ለመለየት” ትጉ፡፡ 

   ነህምያ ያደረገውን ተመልከቱ “ኤልያሴብም በእግዚአብሔር ቤት አደባባይ ለጦቢያ ጓዳውን በማዘጋጀት ያደረገውን ክፉ ነገር አስተዋልሁ፡፡ እጅግም አስከፋኝ፡፡ የጦቢያንም የቤቱን እቃ ሁሉ ከጓዳ ወደ ውጭ ጣልሁ፡፡ ጓዳዎቹንም እንዲያነፁ አዘዝሁ፡፡ የእግዚአብሔርንም ቤት እቃዎች፣ የእህሉንም ቁርባን፣ እጣኑንም መልሼ በዚያ አገባሁ” (ነህ.13፥7-9) ይህ መልእክት ለኛም በዚህ ዘመን ላለን የወንጌል መልእክተኞች የተሰጠ የአደራ መልእክት ነው፡፡ የእግዚአብሔርን ቤት ጓዳዎች እናፀዳ ዘንድ ይገባል፡፡ (ሮሜ.12፥1) ከጦቢያ፣ ከአሮጌው ሰው፣ ከስጋዊ ማንነት የፀዳ፣ የእውነት ዓምድና መሰረት የሆነውንም እውነተኛ የእግዚአብሔር መቅደስ ማግኘት ያስፈልገናል፡፡ ጦቢያ በተቀመጠበት ጓዳ የጠራና የሰባ የመንፈስ መብል የለምና፡፡ 

    መንፈሳዊ ቤት ሆኖ ለመሰራት ጓዳን ማጽዳት አስፈላጊ መሆኑን ልንገነዘብ ያስፈልጋል ፡፡ ጓዳን ማጽዳት ስል ያለ እግዚአብሄር ጸጋ የሚያገለግሉ የሚያስተምሩ የሚሰብኩ የሚዘምሩ እረኛ ነብያት ሃዋርያት የሆኑ እነዚህን ለይተን ማጽዳትና ጸጋው ያላቸውን መተካት ያስፈልጋል ባይ ነኝ ቤቱ አዲስ ሲሆን ልንረሳው የማይገባን ነገር ከአሮጌ ቤት አሮጌ እቃ ለቤቱ እንደማይመጥነው ለአዲሱ መንፈሳዊ ቤትም በአዲስ ቅባት የተቀቡ ለቤቱ የሚመጥኑ የመገልገያ እቃዎች ያስፈልጋሉና ይህንን ነህምያዎች ነቅተው እንዲለዩት ቤቱን እንዲያሳምሩት ያስፈልጋል

   ሌላው ደግሞ ዛሬ ጦቢያ ሆኖ በቤተክርስቲያን የተቀመጠ አላፈናፍን ያለና የእግዚአብሄርን መንፈስ ያዳፈነ የሰው ማንነት፤ ማለትም እኔነት የገነነበት የእኔነት መንፈስ ይሆን ?? የእግዚአብሄር ህዝብ ሆይ ልንነቃ ይገባናል፡፡ ተባረኩልኝ፡፡

ጆሮ ያለው ይስማ !

ይህ የመጨረሻው ደውል የተሰኘው ድህረ ገጽ የማንቂያ ደውል እንደሆነም ያስቡ !

  ካሱ ቦስተን 

    ይህንን ጽሁፍ ወደውት ከሆነ ላይክ በማድረግ እንዲሁም ድህረ ገጹን ሰብስክራይብ ቢያደርጉ ሌሎች ጽሁፎች ሲለቀቁ ወዲያው እንዲደርስዎት ይሆናል። ለሌሎች በማካፈልም የድርሻዎትን ይወጡ።

እንዲሁም ከታች ባሉት ሌሎች ዌብሳይቶች ላይ ያገኙኛል ሊንኩን በመጫን ይፈልጉኝ አመሰግናለሁ።

linkedin.com/in/kassuboston

https://www.instagram.com/kasselsa97

https://www.facebook.com/kasselsa97

thelastbell.com (ይህ የመጨረሻው ደውል ገጽ)